Sunday, November 6, 2016

‹‹የፖሊሲ ለውጥ ከሌለ ግለሰቦችን በመቀያየር ውጤት አይመጣም›› – ተቃዋሚዎች


‹‹የፖሊሲ ለውጥ ከሌለ ግለሰቦችን በመቀያየር ውጤት አይመጣም›› – ተቃዋሚዎች
Addis Admass : ባለፈው ማክሰኞ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ያዋቀሩት ምሁራን የተካተቱበት አዲሱ ካቢኔ፤ ለህዝቦች ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት በትጋት እንደሚሰራ አዳዲሶቹ ተሿሚዎች የገለፁ ሲሆን ተቃዋሚዎች በበኩላቸው፤ ግለሰቦችን በመቀያየር ውጤት እንደማይመጣ ጠቁመው፤ ዋና መፍትሄው የፖሊሲ ለውጥ ማድረግ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
30 አባላት ያሉት የጠቅላይ ሚኒስትሩን አዲስ ካቢኔ በተመለከተ ለአዲስ አድማስ አስተያየት የሰጡት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች፤ የምሁራን መሾምም ሆነ የሰዎች መለዋወጥ ብዙም ውጤት አያመጣም ብለዋል፡፡ “ወሳኙ የፖሊሲ ለውጥ ነው” በማለት፡፡
‹‹ሹመቱ በዶክተሮችና ኢንጂነሮች የተሞላ መሆኑ “የምሁራን ካቢኔ” ያሰኘዋል›› ያሉት አቶ ልደቱ አያሌው፤ ኢትዮጵያ በምሁራን የተሞላ ካቢኔ በማቋቋም በዓለም የመጀመሪያዋ ሳትሆን አትቀርም ብለዋል፡፡ “ካቢኔው በምሁራን መሞላቱ ብቻን ግን ለህዝብ ጥያቄ ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት ያስችላል የሚል እምነት የለኝም” ብለዋል፡፡
አለማቀፍ የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ሃይለ ማርያም በበኩላቸው፤ ውጤት ለማምጣት ወሳኙ የፖሊሲ ለውጥ መሆኑን ጠቅሰው፤ የሠዎች መለዋወጥ ብቻውን ውጤት ያመጣል ብለው እንደማያምኑ ገልፀዋል፡፡ በአዲሱ ካቢኔ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን የተሾሙት ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፤ በተሰጣቸው የኃላፊነት ቦታ አገራቸውን ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀው፤ ካቢኔው ለህዝብ የመልካም አስተዳደር ችግሮችም ሆነ ሌሎች ጥያቄዎች በተገቢው መንገድ ምላሽ ይሰጣል የሚል እምነት እንዳላቸው ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ኃላፊ ሚኒስትር በመሆን የተሾሙት ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ በሰጡት አስተያየት፤ የኢትዮጵያ ሚዲያ ጥራት ያለው መረጃ በማድረስ ህዝቡን በአግባቡ እንዲያገለግል ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ አስረድተዋል። “የአዲሱ ካቢኔ አባላትም፤ ለውጥ ለማምጣት መስራታቸው የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን ግዴታ ነው”
አዲሱ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን  ሚኒስትር አቶ ከበደ ጫኔ በበኩላቸው፤ “ሹመቱ ፈተና ነው፡፡ ፈተናውን በአግባቡ የሰራ፣ በህዝብ ዘንድ ይመሰገናል፤ ፈተናውን በአግባቡ መስራት ያልቻለ ደግሞ ይወድቃል›› ብለዋል፡፡ መንግስትና ህዝብ የጣለብንን እምነት መነሻ አድርገን የህዝቡን ፍላጎት ለማርካት እንሰራለን ያሉት ሚኒስትሩ፤ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከሚገኙ ሙያተኞች ጋር በመሆን የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ ለማቀላጠፍና ተገልጋዮን ለማርካት እንደሚጥሩ ተናግረዋል፡፡‹‹የፖሊሲ ለውጥ ከሌለ ግለሰቦችን በመቀያየር ውጤት አይመጣም›› – ተቃዋሚዎች

No comments:

Post a Comment