Thursday, August 11, 2016

ሰሜን አርማጭሆ ወልቃይት ጠገዴ አርግዟል አርግዟል!


ሰሜን አርማጭሆ ወልቃይት ጠገዴ አርግዟል አርግዟል!

ብዙ መረጃዎችን ከሚያቀብለኝና ከሚያስተምረኝ ዶክተር አሰፋ ነጋሽ አንድ ኢሜል ደረሰኝ፡፡ አየሁት፤ ማለፊያ ግጥም ነው፡፡ ግጥሙ የተጻፈው በግንቦት ፪ሺ ዓ.ም. ሊ.ማ. አበባው ይግዘው ነው፡፡ እኚህ አባት ከስምንት ዓመታት በፊት የጻፉት ግጥም ዛሬ ላይ ሆኜ ሳነበው አሁን ያለውን ሁኔታ እንደ መስታወት ቁልጭ አድርጎ አሳየኝ፡፡ እኔም ተይቤ የሊ.ማ. አበባው ይግዛውን ግጥም ማካፈል ፈለግኩ፡፡ (ያለ ገጣሚው ፈቃድ አንዳንድ አንቀጾች ላይ መጠነኛ ማስተካከያ አድርጌባቸዋለሁ) መልካም ንባብ!!
አይ አገሬ!
አገሬ ራስ-ጋይንት ማማው ደብረ ታቦር፣
የሊቃውንት አምባ የነጋሪት አገር፣
እንዴት በወያኔ ታሪኩ ይደፈር?!
አገሬ አዲስ ዘመን፣ በለሳ ቋሊሳ፣ ዘሐጌና መና፣
እንዳላሳደገ ያንን ሁሉ ጀግና!
ይጫዎትበታል የወያኔ ሙና?!
አይ አገሬ!
ወይ አገሬ ጎንደር የፋሲል መዲና፣
የእነ እያሱ ዙፋን እንዲህ አረጀና፣
በነ ስም አይጠሩ ሆኖ ሊቀር ወና!?
አገሬ አርማጭሆ! ፈልፈልና ተንፈል!
የጀግኖች መፍለቂያ የጎበዞች ክልል!
እንደምን ይደፈር በምንደኛ ምልምል!?
ወይ አገሬ ዳባት! የነጋታው አገር! አገሬ ወገራ!
አገሬ ወፍ አርግፍ! ወልቃይት ጠገዴ! ዳንሻና ኹመራ!
እንደምን ይደፈር በትግሬ ኩታራ!
ወይ አገሬ ጭልጋ! ወይ አገሬ ቋራ!
የአባ ታጠቅ አገር የጀግኖቹ ጎራ!
አገሬ አዳኝ አገር አገሬ መተማ፣
ለኢትዮጵያ አንድነት አካሉ እንዳልደማ፣
እንዴት በወያኔ ታሪኩ ይግማማ!?
አይ አገሬ!
ወይ አገሬ ሰሜን፣ ሰሜን አምባ ራስ፤
የነጋሪት አገር ባለብዙ ቅርስ፣
እንዴት በኩታራ ክብሩ ይገሰስ!?
አገሬ ሰሃላ፣ ወይ አገሬ ጠለምት፣ አገሬ በየዳ፣
ደረስጌ ራስ ዳሸን፣
እንዴት በወያኔ ድንበርህ ይሸንሸን!?
ኧረ ጃሎ በሉ! ጎበዝ ጃሎ በሉ!
ምንሽር ወልውሉ መውዜር አቀባብሉ!
ትናንትን ረስቶ ባንዳው እንዳመሉ!
ተከዜን ተሻግሬ ልግዛ ይላል አሉ!?
ወይ አገሬ ሰሜን አገሬ ወገራ፣
ለጠገበው ጥይት ለራበው እንጀራ፣
ይህ ነበር ታሪኩ በጣም የሚያኮራ፣
በቁም ሊበላህ ነው የራበው አሞራ!
የሚመነጥረው የሚጠርገው ቢያጣ፣
ጎንደርን እንደልብስ ሊቀደው ጋሬጣ!?
ያ መልቲ ወያኔ ይኸው ልብ አግኝቶ፣
በለስ ቀናውና በቋንቋ አዘናግቶ፣
ወልቃይት ጠገዴን፣ ዳንሻና ኹመራን ከዐማራ ለይቶ፣
ሰሊጥ አምርተናል ይበል አፉን ሞልቶ!?
ዕንቋይ ሲቀባትር ወልቃይት ልብ በል አርማጭሆም አድምጥ፣
ትግራይ ያበቅላል ወይ አንድ አገዳ ሰሊጥ!?
ተርቦ ተጠምቶ የሚቀምሰው ሲያጣ፣
ወያኔ ተከዜን ተሻግሮ ሲመጣ፣
ከእንግድነት በቀር መች ነበረው ጣጣ!?
እኚያ ደጋጎቹ፣ አገር ዘበኞቹ የአገሬ ጀግኖች፣
ዘራቸው የት ጠፋ?
ዐይናውጣው ወያኔ ታሪክ ሲያከረፋ፣
ያባቶቹን ርስት ገበሬው ሲቀማ፣
ኹመራ ተመርቶ መቀሌ ሲለማ፣
ምን አለ አርማጭሆ!? ምን አለ ወገራ!? ይህንን ሲሰማ
ለሰሚው ግራ ነው እንዲህ ያለ ነገር፣
የአርማጭሆ ሱሪ! የወልቃይት ሱሪ! የወፍ አርግፍ ሱሪ መቼ እንዲህ ነበረ!
‹‹ሰሜን አርማጭሆ ወልቃይት ጠገዴ፣
ማረሻው ምንሽር መጎልጎያው ጓንዴ!››
የሚለው ቀረርቶ ውሸት ነበረ እንዴ?
‹‹አንበሳ ተኝቶ ጊደር ሸናችበት፣
ከምን ያለው ጊዜ እኛም ደረስንበት!
ያንበሳ ልጅ ሞቶ የጅብ ልጅ ገነነ!
አላሳልፍ አለ ጸጉሩ እየቦነነ››
ይባል የነበረው እውን ዕውነት ሆነ!?
‹‹ውሽልሽል ነው ኧረ ውሽልሽል ነው! ውሽልሽል ነው እርቁ፣
አውድማው ይለቅለቅ በሮቹም አይራቁ፣
እንኳን ከቀያችን ሰተት ብሎ ገብቶ፣
ከሩቁ ያውቀናል ሱዳን መች ዘንግቶ!
የጀግኖቹን ቀየ የሕዝቡን አጽመ ርስት፣
እንዴት እናያለን ሱዳን ሲኮሳበት!?
‹‹የትግራይ ምንደኞች እየተሳሳቡ፣
ግዙን ብንላቸው ሊሸጡን አሰቡ!
ዐማራ ሆይ ስማ፣ ልብህ አያመንታ፣
መሀል ዳር ይሆናል፣ ዳሩ ከተፈታ!››
አይ ዘራፍ!
ኧረ ቆሉብን! ኧረ ፈጩብን!
እንጠብቃለን እስኪያቦኩብን!?
ከዋለ ካደረ አይሰማ የለ!
ድርቡሽ እንደገና ቋራን አቃጠለ!
የአርማጭሆን መሬት ድርቡሽ ተካፈለ!?
ማኅበረ ሥላሴን ገዳሙን ከለለ!?
ምን ትጠብቃለህ ከወያኔ መንጋ?
አካልህን ሲያደርሰው እንደ ደዌ ሥጋ?
ሰሜን አርማጭሆ ወልቃይት ጠገዴ አርግዟል አርግዟል
አልተገላገለም ገና ምጥ ተይዟል!!
ፈራን አላልናቸው? እርዱን አላልናቸው?!
እነርሱን እንደዚህ ምን አስቀዘናቸው?!
ለሱዳን ጥብቅና ማነው ያቆማቸው?
‹‹ተላላ ነው አገር! አገር ተላላ ነው! ይጓዛል እንደሰው፣
በየበሩ ቆሞ ጀግና ታልመለሰው!!››

No comments:

Post a Comment