Wednesday, August 2, 2017

የፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ውሎ source zahabsha

 

     


የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ፕሮጀክት እንደዘገበው:  ዶ/ር መረራ ለዛሬ ሃምሌ 25/2009 ተቀጥረው የነበረው በክሱ ላይ በማስረጃ ዝርዝር የተጠቀሱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን ዝርዝር ለተከሳሽ (ዶ/ር መረራ) ማሳወቅን ወይም አለማሳወቅን በተመለከተ የፌደሬሽን ምክር ቤትን ምላሽ (ትርጓሜ) ለመስማት ነበር።
ሆኖም የ19ኛ ችሎት ዳኞች ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ምላሽ እንዳላገኙ በመግለፅ፤ ፌደሬሽን ምክር ቤት ለህገመንግስት አጣሪ ኮሚቴ ትርጓሜውን እንዲሰራ የላከው ደብዳቤ ግልባጭ እንደደረሳቸው ተናግረዋል።

የዶ/ር መረራ ጉዲና ጠበቃዎች የሚከተለውን ሃሳብ አንስተው ተከራክረዋል። ደንበኛችን ከታሰሩ 9ወር ሆኗቸዋል፤ የተፋጠነ ፍትህ የማግኘት መብታቸው እየተከበረ አይደለም፤ ፌደሬሽን ምክር ቤት የተላከው የትርጉም ጉዳይ ፍ/ቤቱ በራሱ የሚወስነው ነገር ስለሆነ ችሎቱ ራሱ ቢወስን፤ ተመሳሳይ ወንጀሎችን የሚያየው 4ኛ ችሎት ተመሳሳይ ጉዳዮችን ችሎቱ በራሱ ነው የሚወስነው፤ ደንበኛችን ከቆዩበት ጊዜ አንፃር፣ ከእድሜያቸው፣ ካበረከቱት አስተዋፅኦ እና ከጤናቸው አኳያ ክሳቸው በክረምትም እንዲታይ እና አጭር ቀጠሮ እንዲሰጥ ጠይቀዋል።

በሌላ በኩል የዶ/ር መረራ ጠበቃ ዶ/ር ያእቆብ ሃ/ማርያም፤ “የታደሰ የጥብቅና ፈቃድ እና ውክልና እያለኝ ወህኒ ቤቱ ደንበኛዬ ዶ/ር መረራን እንዳላገኝ ከልክሎኛል። ስለሆነም ፍርድ ቤቱ በህገመንግስቱ አንቀፅ 21 መሰረት ደንበኛዬን እንዳገኝ ለወህኒ ቤቱ ትእዛዝ እንዲሰጥልኝ አመለክታለሁ።” ሲሉ አቤቱታቸውን አቅርበዋል።
ዳኞችም የሚከተለውን ውሳኔ ሰጥተዋል። የምስክሮች ጥበቃ አዋጅ እና በፀረሽብር ህጉ አንቀፅ 32 ላይ የተደነገገው ህገመንግስታዊ ትርጉሙ አሻሚ መሆኑን የገለፁት ዳኞች፤ ተከሳሽ የአቃቤ ህግ ምስክሮች የመቅረብ ያለመቅረብን በተመለከተ ያቀረቡትን መቃወሚያቸውን ውድቅ ሚያደርጉ ካልሆነ በስተቀር የፌዴሬሽን ምክርቤትን ትርጓሜ መጠበቅ ግድ መሆኑን ገልፀዋል። 4ኛ ችሎት ተመሰሳሳይ ጉዳዬችን በራሱ ይሰራዋል የተባለውን ጉዳይ በተመለከተ፤ ለሌሎች ችሎቶች ገዢ የሚሆነው ሰበር ሰሚ ችሎት የሚሰጠው ውሳኔ ብቻ መሆኑን ጠቅሰዋል— ዳኞቹ። ክሱ በክረምት እንዲታይ ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ የፍርድ ቤቱ የእረፍት ጊዜ በመቃረቡ እና የዛሬ አመት ክስ የተመሰረተበት መዝገብ ጉዳይ እስከ ነሃሴ 12, 2009 ስለሚያዩ፤ የእነ ዶ/ር መረራን መዝገብ በክረምት ማየት እንደማይችሉ ተናግረዋል።
በዚህም መሰረት የፌዴሬሽን ምክርቤትን ምላሽ ለመጠባበቅ ለጥቅምት 6/2010 ቀጠሮ ሰጥተዋል። የጠበቃ ዶ/ር ያእቆብን አቤቱታ በተመለከተም ለቃሊቲ ማረሚያ ቤት ደንበኛቸውን እንዲያገናኟቸው ትእዛዝ እንዲወጣ ተብሏል።

No comments:

Post a Comment