Thursday, June 29, 2017

በአፋን ኦሮሞ” አማካኝቶ ማስተር ፕላኑን በጓሮ በር – (ከኤርሚያስ ለገሠ) source zhabesha



ህውሃት ለሁለት የተሰነጠቀ ሰሞን ጐልተው ከታዩ ባህሪያት አንዱ የኦህዴድ ካድሬዎች “የኦሮሞ ብሔርተኝነት ” ካርድ የመዘዙበት ነበር። እነ ኩማ ደመቅሳ እና ግርማ ብሩን ጨምሮ በመዘዙት ካርድ “የትግራይ የበላይነት ሊውጠን ነው” በማለት ወደ ስልጣን ጫፍ ( ጠቅላይ ሚኒስትርነት ጨምሮ) ለመቆጣጠር የተጉበት ነበር።
እናም በእነ ግርማ ብሩ የተመራው ቡድን የኦሮሞ ብሔርተኝነት ይቀሰቅሳል ብሎ ያሰበውን እቅዶች በአጭር ጊዜ ውስጥ ይፋ አደረገ። ከእነዚህ ተግባራት አንዱ በአዲሳአባ የሚሰሩ ሥራዎች ተለይተው የቀረቡበት ነበር። ከስራዎቹም ውስጥ አንዱ ” በአዲሳአባ አምስት ዞኖች ውስጥ በሚገኙ 28 ወረዳዎች በአፋን ኦሮሞ የሚያስተምሩ 28 አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች መክፈት” የሚል ነበር። በነገራችን ላይ በወቅቱ አዲሳአባ በአምስት ዞኖች እና 28 ወረዳዎች የተከፈለችበት ነበር።
እነዚህ ትምህርት ቤቶች ተገንብተው እስኪያልቁ አምስቱም ዞኖች በአጣዳፊነት ነባር ትምህርት ቤቶችን በመለየት ለጐልማሶች የማታ፣ ለህጻናት እና ታዳጊዎች የቅዳሜ እና እሁድ እንዲሁም በክረምት ኢ_መደበኛ ትምህርት እንዲጀመር ጥብቅ ኦህዴዳዊ ትእዛዝ ተላለፈ። በድርጅት ቋንቋ መደብ ወረደ። መደቡን ለማስፈፀም ደግሞ የአዲሳአባ ካቢኔ የነበሩት ሊቀመንበር አሊ አብዶ ፣ ሀይሉ ደቻሳ ፣ ወ/ሮ ስመኝ ውቤ( የአፈ ጉባኤ ደግፌ ቡላ ባለቤት እና በኋላ ላይ በአዜብ መስፍን ከም/ል ሚኒስትርነት የተባረረች የምንወዳት እህታችን) እና አምባሳደር ሰለሞን ተመደቡ። ተግባሩ በቁልፍ ደረጃ በመቀመጡ ስራውን ያንጠባጠበ ካድሬ በኦህዴድነት መቀጠል እንደማይችል ተገለፀ።
በየቀበሌው የሚገኝ ካድሬ ቤት ለቤት እያሰሰ የኦሮሞ ዘር አለው የሚለውን አዲስአበቤ እንዲመዘግብ አደረገ። እንደ መሰረተ ትምህርት ዘመቻ ፍቃደኛ ያልሆነውን ማስገደድ ተጀመረ። በደርግ ጊዜ ዝነኛው ቆምጬ አምባው ” አስኳላ የማይሄድ ቡዳ ነው!” ያለውን በተሞክሮ በመውሰድ የአዲሳአባ ኦህዴድ ካድሬዎች ” አፋን ኦሮሞ የማይማር የነፍጠኛ ተላላኪ ነው!” የሚል ማዕከላዊ መልእክት ቀርፀው በጥቅም ላይ አዋሉ።
ስራው በተጀመረ የመጀመሪያው ወር የተመረጡት አምስት ትምህርት ቤቶች በምሽቱ ክፍለ ጊዜ ከጠቅላላው አዲሳአባ በአማካይ 500 ተማሪ ተገኘ። ቅዳሜ እና እሁድ በተዘጋጀው የህጻናት፣ ታዳጊዎች እና ወጣቶች ክፍለጊዜ በአማካይ አንድ ሺህ የሚጠጋ ተገኙ። የኦህዴድ አብዮታዊ ካድሬዎች አጀማመሩ ጥሩ እንደሆነ ገመገሙ።
ስራው በተጀመረ ሶስተኛው ወር የምሽቱ 60 ፣ የሰንበቱ ወደ 90 ተማሪ ብቻ ቀረ። አምስቱ ትምህርት ቤት ታጥፈው በዞን ሁለት ውስጥ ወደ ሚገኘው ተግባረ እድ ትምህርት ቤት እንዲጠቃለል ተደረገ። በአራተኛው ወር እንደ ኮንደሚኒየም ወደ 40/60 ተቀየረ። አካሄዱ አስደንጋጭ የሆነበት ኦህዴድ ” ሁሉም ዜሮ ዜሮ” መመዝገቡ በፊት ትምህርቱ ባልተገለፀ መመሪያ እንዲቀር ተወሰነ።
ከሁሉም የሚገርመው ነገር አዲሳባ የሚኖር አንድም የኦህዴድ ባለሥልጣን ልጆቹን አፋን ኦሮሞ እንዲማሩለት አልሰደደም። በክረምቱ ክፍለጊዜም ሆነ በሰንበት ባለሥልጣናት ልጆቻቸውን የሚልኩት የእንግሊዘኛ እውቀታቸውን የሚሳድጉበት ከ3ሺህ ብር በላይ የሚከፈልባቸው ውድ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ትምህርት ቤቶች ነበር። አንዳንዶቹ ከቋንቋው በተጨማሪ ልጆቻቸው እንዲዝናኑ የሚልኩት ወደ ትውልድ ገጠሪቱ ኢትዮጵያ ሳይሆን ወደ ሰሜን አሜሪካ እና አውሮፓ ነበር ። አሁንም የተቀየረ ነገር ያለ አይመስለኝም። እንደውም እየሰማን ያለነው በሌብነት እና መሬት ችብቸባ ኪሳቸው ያበጠ የኦሮሚያ ዞን እና ወረዳ ካድሬዎች ልጆቻቸውን የሚያስተምሩት አዲሳባ ቤት ተከራይተው እጅግ በጣም ውድ በሆነ ” ከእንግሊዘኛ ውጭ መናገር ክልክል ነው!” የሚል ማስታወቂያ የተለጠፈበት ትምህርት ቤት እንደሆነ ነው። ተወደደም ተጠላ መሬት ላይ ያለው እውነታ ይሄ ነው።
ከአዲስአባ አወቃቀር አኳያም የተቀየረ ነገር የለም። አዲስአበቤ እንኳን በሕውኃት ድርጅታዊ መመሪያ የተላከለትን ቀርቶ ሌላውንም ቢሆን በጥሞና የሚመለከት አስተዋይ ህዝብ ነው። (” ወርቅ ህዝብ ነው!” ብዬ ልገልፅ ነበር፣ ኩረጃ ይመስልብኛል ብዬ ተውለኩት።) ያለማጋነን አዲስአበቤ የህውሓትን አካሄድ እና አላማ ከመገንዘብና ከመታገል አኳያ የቀደመው የለም።
እናም ዛሬ ” የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ” በሚለው አባይ ፀሐዬና በረከት ስምኦን የፃፈው አዋጅ ላይ ” አስተዳደሩ በአፋን ኦሮሞ ልጆቻቸውን ማስተማር ለሚፈልጉ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ማደራጀት አለበት” የሚል ተፅፎ ስመለከት የተሰማኝ ከላይ የተገለጠው ነው። እነ አባይ በዚህ አዋጅ አማኸኝተው ማስተር ፕላኑን በጓሮ በር ማስገባታቸው እንዳይታወቅ “የዶሮን ሲያታልሏት” ማታለያ ይዘው ብቅ ማለታቸው እርስ በራስ ለማጋጨት ነው። ሌሎች የህጉ እሳቤዎች መሰረታዊ ምንጫቸው ይሄ እና ይሄ ብቻ ነው።

No comments:

Post a Comment