Thursday, October 26, 2017

የሀገሪቱ ጦር እና ደህንነት የህወሓትን ስልጣን በማዳን ስራ ላይ አተኩሯል source zehabesha

(ቢቢኤን) በኢትዮጵያ የሚገኙው ማንኛውም ዓይነት ጦር እና የደህንነት አካል የህወሓትን ስልጣን ለመታደግ አተኩሮ እየሰረ እንደሚገኝ ምንጮች ጠቆሙ፡፡ የሀገሪቱ የደህንነት እና የመከላከያ ሰራዊት ቁልፍ ቦታዎች በህወሓት እጅ ውስጥ እንደመገኘቱ፣ የፓርቲውን ዕድሜ ለማራዘም ከመቼውም ጊዜ በላይ እየተሰራ እንደሚገኝ ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ ለዚህም ሲባል መደበኛ ስራቸው ሀገር መጠበቅ የሆነ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ህዝባዊ ተቃውሞ በተነሳባቸው ቦታዎች ጭምር እየሔዱ በህዝብ ላይ ጥቃት እየፈጸሙ እንደሚገኙ መረጃዎች በመጠቆም ላይ ናቸው፡፡

ከሁለቱ አካላት በተጨማሪ ደግሞ በህወሓት ርዕዮተ-ዓለም ቅርጽ የተመሰረተው የአጋዚ ጦርም እንደተለመደው፣ የስርዓቱን ዕድሜ ለማስቀጠል ግድያን ጨምሮ ማንኛውንም ዓይነት አረመኔያዊ እርምጃ እየወሰደ ይገኛል፡፡ የኦሮሚያ ፖሊስ ከዚህ ቀደም ከነበረው አኳኃኑ የተወሰነ መሻሻል ማሳየቱ እና ለተቃውሞ አደባባይ ከሚወጡ ሰዎች ጋር መግባባት መፍጠሩ ህወሓትን አላስደሰተውም ይላሉ- ታዛቢዎች፡፡ ለዚህም ሲባል የአጋዚ ጦር ተቃውሞ በሚነሳባቸው የኦሮሚያ ከተሞች እየገባ ግድያ እንዲፈጽም እየተደረገ ይገኛል ብለዋል-ታዛቢዎቹ፡፡
የህወሓት መንግስት ጀምበር እየጠለቀችበት እንደሚገኝ የሚናገሩ አስተያየት ሰጪዎች፣ ስርዓቱ የባከነ ሰዓት ላይ የሚገኝ እንደመሆኑ ማንኛውንም ዓይነት እርምጃ ከመውሰድ እንደማይመለስ ያክላሉ፡፡ ቀስ በቀስም ሀገሪቱን ወደ ወታደራዊ ስርዓት ሊወስዳት እንደሚችልም አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡ በተለይ በህወሓት እጅ የሚገኙት ዋና ዋና የደህንነት እና የመከላከያ ቦታዎች፣ አሁን ላይ ስርዓቱ እንዴት ብሎ ከመጣበት ህዝባዊ መዓት ማምለጥ እንዳለበት በሰፊው እየመከሩ እንደሆነ ከምንጮች ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡ በየቀኑ እየተካሔዱ ባሉ ተቃውሞዎች የተነሳ ፋታ ያጣው የህወሓት መንግስት፣ አሁን ላይ ሌሎችን ገድሎ ራሱን ለማዳን እየተፍጨረጨረ ይገኛል፡፡

No comments:

Post a Comment