Monday, November 20, 2017

ጎንደር በሚገኙት የወያኔ ባለስልጣናት ላይ ጥቃት ተሰነዘረ | አዘዞ ወታደራዊ ካምፕ እና ኤርፖርት መስመር ታምሷል! source zehabesha

ለጥቃቱ በህቡእ የቆየ ድርጅት ሃላፊነት ወስዷል!
ሙሉነህ ዮሐንስ
ቅዳሜ ህዳር 9 2010 እኩለ ሌሊት ሲሆን ጎንደር አዘዞ ውስጥ በተመሳሳይ ሰአት በሁለት ቦታ በወያኔ ላይ እርምጃ መውሰዱን በህቡ ስንቀሳቀስ ቆይቻለሁ ያለ ድርጅት በላከልን መልእክት አሳወቀ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ፓርቲ(ኢብፓ)/Ethiopian National Party የላከውን መግለጫ ዝርዝሩን እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
የኢብፓ ወታደራዊ ክንፍ ሁለት ፍንዳታ ነው የፈፀምኩት ያለው። አንደኛው ጥቃት አዘዞ 24ተኛ ክፍለ ጦር ካምፕ ላይ ነው። በጥቃቱ በውስጡ ምን እንደያዘ ያልታወቀ መጋዘን ጋይቷል። በወታደሩ ላይ ከፍተኛ ትርምስ ፈጥሯል። ዋናው የጥቃቱ ኢላማ የሆነው ግን ሁለተኛው ጥቃት ነው። ድርጅቱ ቀድሞ ባገኘው ጥብቅ መረጃ መሰረት ጨለማን ተገን አድርገው በእኩለ ሌሊት አዘዞ ወደ ሚገኘው ኤርፖርት በሁለት ዘመናዊ ኮብራ መኪኖች ሲጓዙ አዘዞ በሚገኝ ድልድይ አካባቢ ሲደርሱ የእጅ ቦንብ ተወርውሮባቸዋል። ተከታትሎ ተኩስ ስለተከፈተባቸው በፍጥነት ወደ ኋላ ዞረው ወደ ጎንደር ከተማ እንዲመለሱ ተገደዋል። በመኪኖቹ ውስጥ የነበሩትን የህወሃት ባለስልጣናት ማንነትና የደረሰባቸውን ጉዳት ለጊዜው መለየት አልተቻለም።
24ተኛውና 42ተኛው ክፍለ ጦሮች የሰፈሩበት ካምፕ ላይ የተጣለው የመጀመሪያው ጥቃት አቅጣጫ ማሳቻ ነበር። የደፈጣ ጥቃት የተፈፀመበት ድልድይ ወደ መተማ መስመር መገንጠያ ላይ ነው። ሃላፊነት የወሰደው ኢብፓ ጠላትን ከፍ ባለ ደረጃ ለመፋለም ያለንን ወኔና ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ብሏል።
በቂ ቅድመ ዝግጅት በመደረጉ ታጋዮቹ በቀላሉ ወደ ቦታቸው ተመልሰዋል። ለደሞዝ ሲል ለወያኔ አገልጋዩ ወታደር ከፍተኛ የሆነ ድንጋጤ አድሮባቸዋል። ከእኩለ ሌሊት ጀምሮ አሰሳ እየተደረገ ነው። የወያኔ አመራሮች ተሸብረዋል። በአጠቃላይ ጎንደር ላይ ከፍተኛ የሆነ ውጥረት ተፈጥሯል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ፓርቲ የወያኔን እብሪት አንታገሰውም ቀጣይና ተከታታይ እርምጃ እወስዳለሁ ብሎ ማስጠንቀቂያ ልኳል።
ድርጅቱ በተለያየ አደረጃጀት በስፋት በገጠርም በከተማም ሲታገሉ የቆዩ ሃይሎችን ወደ አንድ ወጥ አደረጃጀትና አመራር ማሰባሰቡን እንዲሁም መሰል ቀጣይ ተግባራት በመላ ሃገራችን እንደሚቀጥል አስታውቋል።
ድርጅቱም አመራሩም ሙሉ ለሙሉ በህቡእ ሃገር ውስጥ እንደሚንቀሳቀስ ስለ ገለፀው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ፓርቲ አላማና ማንነት የድርጅቱ ማኒፌስቶ ስለደረሰን በቀጣይ እንዘግባለን።

749 Shares
Share
Tweet
Pin
Email
Share

No comments:

Post a Comment