Sunday, July 2, 2017

ሁከት አንስተዋል የተባሉ እስረኞች ከቅሊንጦ እስር ቤት ወደ ሌሎች እስር ቤቶች ተዛወሩ source zhabesha

file photo
የፍኖተ ዴሞክራሲ ዜናና ኃተታ –
ርዕሰ ዜና

#ሁከት አንስተዋል የተባሉ እስረኞች ከቅሊንጦ እስር ቤት ወደ ሌሎች እስር ቤቶች ተዛወሩ
#አመጽ ቀስቃሽ ግጥሞችን በዩቲዩብ አሰራጭተዋል የተባሉ ጋዜጠኞች ክስ ተመሰረተባቸው
#በጎንደር አንድ የሞርታር ጥይት ፈንድቶ በህይወትና በአካል ላይ ጉዳት አደረሰ
#ሳኡዲ አረቢያ የጣለችውን የቀን ገደብ ለ30 ቀን አራዘመች
#በአገራችን የገባው የተምች መንጋ በከፍተኛ ፍጥነት መስፋፋቱ አሳሳቢ ነው ተባለ
##ዝርዝር ዜናዎች##

#በቅሊንጦ ከሚገኘው የወያኔ እስር ቤት ውስጥ ከ20 የሚበልጡ እስረኞች ወደ ዘዋይ እስር ቤት ቁጥራቸው ያልታወቀ ሌሎች ደግሞ ወደ ሸዋ ሮቢት የተዛወሩ መሆኑ ታውቋል። እስረኞቹ ወደ ሌሎች እስር ቤቶች የተዛወሩበት ምክንያት በመካከላቸው በዘር ላይ የተሰመረተ ግጭት ፈጥረው ሁከት በማስነሳታችው ነው የሚል ምክንያት እየተሰጠ ሲሆን ከተዛወሩት መካከልም ከዚህ በፊት #እስር ቤቱን በማቃጠል የተከሰሱ እንዳሉበት ለማወቅ ተችሏል። ላለፉት ጥቂት ቀናት በቅሊንጦ እስር ቤት ዞን 4 እና 5 ውስጥ የታሰሩ እስረኞች ዘመዶቻቸው እንዳያዩዋቸው የተከለከሉ መሆናቸውም ታውቋል። እስር ቤት ውስጥ የታጨቀው እስረኛ በጣም በርካታ ከመሆኑ የተነሳ እስረኞች በጥበቱ የተማረሩ መሆናቸውን በተደጋጋሚ መግለጻችው ይታወቃል። በ 900 ሚሊዮን ብር እየተሰራ ነው የሚባለውም እስር ቤት ምን ያህል ችግሩን ሊያቃልል እንደሚችል አልታወቀም ተብሏል።
#በጋዘጠኛነት ሙያ ተሰማርተው የነበሩና አመጽ ቀስቃሽ ግጥሞችን በዩቱዩብ አሰራጭታችኋል የተባሉ ሰባት ሰዎች ክስ የተመሰረተባችው መሆኑ ታወቀ። ሰባቱ በዛሬው ዕለት ፍርድ ቤት ቀርበው የተሰነሰዘረባቸው ክስ የተሰማ ሲሆን ከተከሳሾች በኩል የሚቀርበውን የመጀመሪያ የመቃወሚያ ሀሳቦችን ለመሰማት ለሐምሌ 7 ቀን ቀጠሮ የተያዘ መሆኑ ታውቋል።
#በጎንደር ከተማ ቅዳሜ ከተማ ውስጥ ልዩ ስሙ አሮጌ ብረት ተራ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ የሞርታር ጥይት በመፈንዳቱ ምክንያት ሁለት ስዎች ህይወታቸውን ያጡ መሆናቸውና ሌሎች ሶስት ሰዎች የቆሰሉ መሆናችው ተነገረ። የሞርታር ጥይቱን ለብረት ሙቀጫ ለማዋል በብረት መጋዝ በመቁረጥ ላይ እንዳሉ ጥይቱ በመፈንዳቱ ሰዎቹ ወዲያውኑ ሊሞቱ የቻሉ መሆናቸው ተነግሯል።
#የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ህገ ወጥ ናቸው የሚላቸው ስደተኞች ከአገሩ እንዲወጡ አውጆት የነበረውን የቀን ገደብ ለ 30 ቀናት ያራዘመው መሆኑን ገለጸ። ለቀን ገደቡ መራዘም በሳኡዲ መንግስት በኩል የተሰጠ ማብራሪያ ባይኖርም የወያኔ አገዛዝ እና አንዳንድ ወገኖች ላቀረቡት ጥያቄ የተሰጠ መልስ ሳይሆን አይቀርም የሚል ግምት አለ። በሳኡዲ አረቢያ ከ400000 እስከ 450000 ሺ የሚገመቱ ኢትዮጵያን ስደተኞች በህገ ወጥ መንገድ ይኖራሉ ተብሎ ሲገመት እስካሁን የተመለሱት ቁጥር ከ45000 እንደማይበልጥና የመጓጓዣ ሰነድ ተሰጥቷቸዋል የተባሉት 111 ሺ ብቻ መሆናቸው ተነግሯል።
#በአገራችን የገባው የተምች መንጋ በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ በመሄዱ ሁኔታው በጣም አሳሳቢ መሆኑ ተነገረ። እስካሁን ድረስ በ35 ዞኖች በ136 ሺ ሄክታር መሬት ላይ የተዘሩ ሰብሎችን ያበላሸው ይኽው የተምች መንጋ በቅርቡ እስከሁለት ሚሊዮን ሄክታር በሚድርስ ቦታዎች ላይ የተዘሩትን አዝርዕት ሊያበላሽ እንደሚችል ተገምቷል። ይኽም በአገሪቱ ውስጥ ለእርሻ ተስማሚ ከሆኑ መሬቶች መካከል አንድ ስድሰተኛ የሚሆን ሲሆን ተምቹ የሚያደርሰው ጥፋት የረሃቡንና የድርቁን ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ ሊያስፋፋው ይችላል ተብሎ ተሰግቷል። ተምቹ በሰዓት ከ 100 ኪሎ ሜትር በላይ የመብረርና በአንድ ጊዜ 1500 እስከ 2000 እንቁላል የመፈልፈል አቅም እንዳለው ባለሙያዎች ይናገራሉ። በወያኔ የእርሻና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስተር ተምቹን ለማጥፋት የተደረገው ጥረት የተወሰነ ውጤት ቢኖረውም ተምቹን ለመቆጣጠር ያልተቻለ በመሆኑ በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ይገኛል።

የሕወሓት መንግስትን ከድተው በኤርትራ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ኃይልን የተቀላቀሉት ወታደሮች ምስጢር ማውጣት ጀመሩ source zhabesha



የሕወሓት መንግስትን ከድተው በኤርትራ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ኃይልን የተቀላቀሉት ወታደሮች ምስጢር ማውጣት ጀመሩ

Thursday, June 29, 2017

የሕወሓት የስንብት ዐዋጅ (ምሕረት ዘገዬ) source ecadef

ምሕረት ዘገዬ
ሰሞነኛው ሕወሓታዊ  የዕውር ድምብር እንቅስቃሴ ብዙ ነገሮችን እንዳስታውስ አድርጎኛል፡፡ እውነቱን ለመናገር ይህንን አዲስ አበባን ለኦሮሞ የመስጠት ጉዳይ በዩቲዩብ ስመለከት ከመደንገጥም አልፌ ከሦስት ቀናትም በኋላ አሁን ድረስ ላልተወኝ ራስ ምታት መጋለጤን ልደብቅ አልፈልግም፡፡ የዕብድ ሥራም አንዳንዴ ያስደነግጥና እስኪለቅ ድረስ መቸገር ይኖራል፡፡ የድንጋጤየ ዋና መነሻ የወያኔው ዕብደት የወለደው ይህ ሕዝብን የማተረማመስ ሥልት ከቁም ነገር የሚጣፍ ሆኖ ሣይሆን ከወኔያው ታሪክ በመነሣት ብዙ “አይሆኑም” የሚባሉ ነገሮች በመሆናቸው እነዚህ ውሉዳነ አጋንንት የቆይታ ዕድል ካገኙ ይህም ቅዠት እውን ሊሆን እንደሚችል በመጠራጠር ነው፤ “ጠርጥር ገንፎም አለው ስንጥር” ይባላልም እኮ፡፡ እንጂ እንዲህ ያለ ዘመኑን ያልዋጀ የዕብደት ዐዋጅ ኢትዮጵያን ያሰጋታል ብዬ ከልቤ አምኜበት አይደለም፡፡(በነገራችን ላይ ኤርምያስ ለገሠ በዚህ ነገር ዙሪያ የጻፈው ግሩም ወቅታዊ  ሀተታ አለና ያላነበበ ሰው ቢያነበው ጥሩ ነው እላለሁ፡፡)
ይህ ክስተት ከሚያስታውሱኝ በጣም በርካታ ነገሮች ውስጥ አንድ ሁለቱን ያህል ላስታውሳችሁ፡፡
ከምድራዊው ልጀምር፡፡ በትዳር ሕይወቷ ብዙ ልጆችን ያፈራች አንዲት የቤት እመቤት በጠና ትታመምና ንስሃ ለመግባት በዚያውም የኑዛዜ ቃሏን በእማኞች ፊት ለመስጠትና ይህችን “ቆሻሻ” ምድር ለመሰናበት ሁለት ሽማግሌዎችንና የነፍስ አባቷን ታስጠራለች (አሉ)፡፡ የተባሉት ሰዎች መጥተው ያችን እንደወያኔ በፅኑ ጣዕር ወህማም ላይ የነበረችን ሴትዮ በመክበብ ማዳመጥ ይጀምራሉ ፡፡ የአሥራ አንድ ልጆች እናት የሆነችው ወይዘሮ በቅድሚያ ንስሃዋን ማውረድ የፈለገች ይመስላል፡፡ እናም ቀጠለች – “መምሩ ደህና አድርገሁ ይፍቱኝ፤ በደምብ ይጸልዩልኝ፡፡ በቁርጥ ስለተያዝሁ እውነቱን ብቻ ነው የምናገረው፡፡ ለትዳሬ ታማኝ አልበርሁም፡፡ … የመጀመሪያው ልጄን የወለድሁት ከጎረቤታችን ከአቶ አውግቼው ነው፤ ሁለተኛውን ልጄን የወለድሁት ከአጥቢያ ዳኛው ከአጋፋሪ እንደሻው ነው፤ ሦስተኛውን ልጄን የወለድሁት ከባለቤቴ ነው፤ አራተኛውን ልጄንም የወለድሁት ከራሱ ከባለቤቴ ነው፤ … አምስተኛውን ልጄን የወለድሁት ከርስዎ ከራስዎ ከመምሩ ነው፡፡…” ሴትዮዋ አልጨረሰችም፤ የሕወት ድርሣኗን ከፍታ እውነትና እውነቱን ብቻ እየተናዘዘች ነበር፡፡ ሴትዮዋ በመጨረሻ የተናገረችውን ያልሰሙ በመምሰልና ለማመንም በመቸገር ጭምር ሽማግሎቹ ተደናግጠው “ምን አለች፣ ምን አለች?” ብለው እርስ በርስ ይጠያየቃሉ፡፡ ይህችን ጠባብ ዕድል ያገኙት የንስሃ አባት “ኧረ ገና ብዙ ትዘባርቃለች!” በማለት ሰዎቹ በቄሱ ላይ ያሳደሩትን ጥርጣሬን የተሻገረ የውስልትና ሥራ ለማስቀየስ ይሞክራሉ፡፡ ይህን ለማለት ያበቃቸው አለሥራቸው ታምተው ሣይሆን “ሴትዮዋ በጣር ስላለች የምትለውን አታውቅም” ለማለት ፈልገው ነው፡፡ አለቃ ገ/ሃናም ያመለጣትን እውነተኛ ፈስ እንዳልፈሳች ለማስመሰል ስትል በአፏ “ጡጥ!” ያደረገችዋን መንገደኛ “ይቺ ሌላ፣ ያቺ ሌላ” ሲሉ እንደነቁባት መግለጻቸውን እዚህ ማስታወስ ሳይገባኝ አይቀርም፡፡ የምትደበቅ እውነት እንደጭስ ናት – እንደምንም ብላ መውጣቷ አይቀርም፡፡
ለማንኛውም ወያኔ ገና ብዙ ይዘባርቃልና በጥንቃቄ መከታተል ተገቢ ነው፡፡ እነሱ ፈንጂ ባጠመዱ ቁጥር፣ እነሱ ወጥመድ በዘረጉ ቁጥር፣ እነሱ ጉድጓድ በቆፈሩልን ቁጥር እየዘለልን የምንገባ ከሆነ ስህተቱ የኛ እንጂ የነሱ አይደለምና በሚያልፍ መጥፎ ዘመን የማያልፍ ጠባሳ በታሪክ ስንክሳር ላይ ላለመተው ብዙ ጥንቃቄ ማድረግ ያለብን እኛ ብዙኃኑ ነን፡፡ እመለስበታለሁ፡፡
ሰማያዊውን ልቀጥልና ወደ ቁጭቴ(ማጠቃለያየ) ላምራ፡፡ በክርስትናው እምነት እንዲህ ያለ ታሪክ አለ፡፡ መላእክት ፈጣሪን ቅዱስ እግዚአብሔርን በመንበሩ ያጡታል፡፡ ይደናገጣሉ፡፡ ያኔ የመላእክት አለቃ የነበረው ሊቀ ሣጥናኤል የመላእክቱን መደናገጥና የተፈጠረውን ክፍተት በመረዳት በእግዚአብሔር ዙፋን ላይ ሄዶ ይቀመጣል፡፡ ዱሮም ይቀና ነበር ማለት ነው፡፡
መላእክቱ “ማን ነው የፈጠረን?” ብለው ይጠይቃሉ፡፡ ሊቀ ሣጥናኤልም “እኔ ፈጠርኳችሁ!” ይላቸዋል፡፡ ያመኑት አመኑ – በርሱም “ቆርበው ዳኑ”፡፡ ያላመኑት ግን “ፈጣሪያችንን እስክናገኝ በያለንበት (በጽናት) እንቁም!” ብለው ይወስናሉ፡፡ በወቅቱና አሁንም ቢሆን በኃያልነቱና በእልኸኝነቱ የማይታማው ሊቀ ሣጥናኤል እንደተነቃበት ሲረዳ እልህ አስጨራሽ ፍልሚያ/ጦርነት ውስጥ ይገባና በየዋህነትም ይሁን በክፉ መንፈስ ተነድተው ፈጣሪያቸውን የካዱ መሰል መላእክት ጋር በመሆን በዓላማቸው ጸንተው ለፈጣሪያቸው ከቆሙት እነቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ጋር ክንፋቸውን እየተነጫጩ በጨበጣ ይተጋተጉ ያዙ፡፡ በዚያ ታላቅ መንፈሣዊ ጦርነት እግዚአብሔር ባይደርስላቸው ኖሮ አሁን ዓለማችንን በታላቅ ግዳይነት አጋድሞ እየተጫወተባት የሚገኘው ሊቀ ሣጥናኤል ሊያሸንፋቸው ተቃርቦ እንደነበር የሃይማኖት አባቶችና መጻሕፍት ያስተምሩናል፡፡ ግን ያቺ የፈተና ጊዜ አልፋ ዳፋዋ ግን ለአዳምና ሔዋን ደርሳ በነሱም ሳቢያ ወደኛ ተላልፋ ይሄውና በሕወሓት አማካይነት ሌላ ኢትዮጵያዊ የመጨረሻ ፍልሚያ ውስጥ ገብተናል፡፡
አንደናገጥ፡፡ ብዙ ሰው የተደናገጠ ይመስላል፡፡ ብዙ ሰው ደግሞ እንደቀልድ እያዬ ይዝናናበት ጀምሯል፡፡ እንዳንደናገጥ የምመክረው ወያኔ ካርዶቹን ሁሉ አሟጦ ተጠቅሞ( አብዛኛውን በድርቅናና ሳናምንለት ነው) እዚህች የማትረባ ካርድ ላይ በመድረሱና ይህችም ካርድ እርባናቢስ በመሆኗ ነው፡፡ ወያኔና እግዚአብሔር፣ ወያኔና የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ወያኔና እውነት፣ ወያኔና ሰብኣዊነት… በቅጡ ሳይተዋወቁ እነዚህ እርጉሞች ሊሰናበቱ መቃረባቸው ግን በእውነቱ ያሳዝነኛል – “ሰው”ነትን አውቀውና ሆነውም ቢያዩት ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ከልጅነት እስከ ዕውቀት፣ ከጉርምስና እስከ ጉልምስና፣ ከወመሽነት እስከ ጅጅትና ፈጣሪንና የኢትዮጵያን ሕዝብ ማወቅ አለመቻል የአለመታደል ሁሉ ጫፍ ነው፡፡ ይህ ሁሉ የዐዋጅ ጋጋታም አንዱና ምናልባትም ትልቁ የድንቁርናቸው ምልክት ነው፡፡ አንድ ሰው እየሞተ እንኳን ልብ ካልገዛና ወደሰውነቱ – ወደኅሊናው ካልተመለሰ – በስም እንጂ በግብር ሰው መሆኑ ያጠራጥራል፡፡ ለምሣሌ ወያኔዎች አዲስ አበባ እንደገቡ ሰሞንና ከዚያም በኋላ ከኢትዮጵያ ሕዝብ የዘረፉትን የጥቁር አንበሣ ጄኔሬተር፣ የጎንደር ከተማ (ሆስፒታል?) ጄኔረተር፣ የአዲስ አበባ ዳቦ ቤቶች(ከኤርምያስ ሁለተኛው መጽሐፍ እንዳነበብኩት፣ በቢሊዮኖች ብር የሚገመት የመንግሥትና የግል ድርጅቶችን ሀብትና ንብረት … ቢቻል መመለስ ባይቻል መጸጸትና ለመካስ መሞከር ካልቻሉ በርግጥም እንደተወለዱ ሞቱ ሊባሉ የሚገባቸው የሰው ጭንጋፍ ናቸው፡፡ ይህን የቤት ሥራ ለትግራይ ክፍለ ሀገር ብንሰጥ የምንችል ይመስለኛል፡፡
አዲስ አበባ መተተኛ ከተማ ናት፡፡ አዲስ አበባ ልትለውጣቸው ያልቻለቻቸው ሕወሓትን የመሰሉ የጨለማው መንግሥት ወኪሎችን እንጂ ተራ ዜጋን በደቂቃዎች ውስጥ ለውጣ ክፉዎችን ገር፣ ተንኮለኞችን የዋህ የምታደርግ ግሩም ከተማ ናት፡፡ አንድ ሰው ከየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ ይምጣ፣ የትኛውንም ኢትዮጵያዊ ቋንቋ ይናገር አዲስ አበባ ሲደርስ አዲስ አበቤ እንጂ ጎጃሜ ወይም ሸዌ፣ ወሎዬ ወይም ጎንደሬ፣ ወለጌ ወይም ሐረሬ … አይሆንም፡፡ ለልጆቿ ልዩ ፍቅር ያላት፣ ገዢዎች ጣልቃ እስካልገቡባት ድረስ በተቻላት መጠን ሁሉንም ልጆቿን በእኩል ዐይን የምታይ፣ ልዩ መስተጋብር ያላት፣ ልዩ የመቻቻልና የመደጋገፍ፣ የመተሳሰብና የመተዛዘን መንፈስ ያረበበባት በውነትም ልዩ ከተማ ናት – የኔ አዲስ አበባ፡፡ ሁሉንም ሆና፣ ስለሁሉም ተጨንቃና ተጠባ የሁሉንም ስሜት ገዝታ ከክፉዎቹ ገዢዎቿ መዳፍ ምሥኪን ልጆቿን ጠብቃ የምትኖር ከተማ ከአዲስ አበባ ውጪ ብዙም አላውቅም፡፡
አንድ ወቅት እንዲህ ሆነላችሁ፡፡ አንድ ሽማግሌ ከሰሜን ሸዋ ወደ አዲስ አበባ የሚመጡበት የፍርድ ቤት ሙግት ነበራቸው፡፡ ቀጠሯቸው እየተራዘመ ሲሄድ አንድ ችግር ገጠማቸውና ለችሎቱ አቤት አሉ፡፡ “ክቡር ፍርድ ቤት፣ ውኃየ አልቆብኛልና በእግዜር ይሁንባችሁ ዛሬ ፍረዱልኝ ወይም ፍረዱብኝ!” ብለው ያመለክታሉ፡፡ የመሃል ዳኛውም “የምን ውኃ ነው ያለቀብዎት?” ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ እርሳቸውም “‹የአዲስ አበባ ውኃ አይለቅም‹ ሲባል ሰማሁ፤ ቤት ንብረቴን የትሚናቸውን ጥዬ እዚሁ መቅረት ስላልፈለግሁ የምጠጣውን ውኃ ታገሬ ተመንዝ ነው ይዤ የመጣሁት፡፡ የዚህን አገር ውኃ እዚሁ እንዳያስቀረኝ በመፍራት አልጠጣም፡፡…” አዎ፣ ዳኞቹ ተሳስቀው ወዲያዉኑ ወሰኑላቸው ይባላል፡፡ አዲስ አበባ ፍቅሯ እስከዚህ ነው፡፡
የአዲስ አበባን ባለቤትነት እንኳንስ ሕወሓት ዋና አዛዡ ዲያብሎስም አያገባውም፡፡ እንኳንስ ተላላኪው ሕወሓት የርሱ አለቆች ነጫጭባዎቹም አያገባቸውም፡፡ ይህች ታሪካዊት ከተማ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀብት እንጂ፣ የአፍሪካውያን የጋራ ንብረት እንጂ፣ የዓለማችን ሕዝብ የወል ገንዘብ እንጂ ከ90 ጎሣና ነገድ ለአንዱ ወይ ለሌላው በገጸ በረከትነት የምትሰጥ ቁስ አካል አይደለችም፡፡ የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንዲሉ …. የለም … የለም… ተረቱ ልክ አይደለም – ባይሆን “በሰው ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል” ቢባል ይሻላል፡፡ ለማንኛውም ወያኔዎች ስለተጨነቁ አይደለም እንዲህ ያደረጉት፡፡ ወያኔዎች ይህን ያደረጉት በተለይ ኦሮሞንና አማራን፣ በአጠቃላይ ደግሞ ኦሮሞንና ሌላውን ኢትዮጵያዊ ለማባላት ብቻ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የተበላ ዕቁብ ው፡፡ አንዳንድ ጅላጅሎችና ወያኔ-ተከል መሠሪዎች ግን እዚህና እዚያ እንደማይጠፉ መጠቆም ብቻ ሣይሆን በርግጠኝነት እንዳሉ ተረድተን ምንም ኃይልና ጉልበት ሳናባክን በጥርሳችን ብቻ እየሳቅንባቸው ቀኒቷን እንጠብቅ፡፡ እኛ ግን አደራችሁን በከፍተኛ ደረጃ እንጠንቀቅ፡፡ “እንዲህ ልጠግብ በሬየን አረድሁ” እንዳለችው ነፈዝ ሴት ላለመሆን የምንሠራውንና የምንሆነውን እያሰብን እንሥራ፣ እንሁንም፡፡ ሲያልፍ ለሚቆጭ ነገር እንዳንዳረግ እንትጋ፡፡
የኢትዮጵያ ነፃነት አንድ ቦታ እየተሠራች ነው፡፡ ያገሬ ገበሬ “ሳለ ፈጣሪ አሟጠሸ ጋግሪ!” የሚለው በፈጣሪው ዕፁብ ድንቅ ተዓምራዊ ሥራ ስለሚተማመን ነው፡፡ ስለዚህም በሰብኣዊ የውሱንነት ባሕርይ ምክንያት የመምጫዋን ጊዜና የምትመጣበትን አቅጣጫ ለይቼ ማወቅ ባልችልም ነፃነታችን እጅግ ቀርባለች፡፡ ንፋሷ አልባብ አልባብ በሚለው መለኮታዊ መዓዛው እያወደኝ ነው፡፡…
እመለስበታለሁ ወዳልኩት ነገር ልመለስ፡፡ ወገኖቼ! “ዐይጥ ወልዳ ወልዳ ጅራቷ ሲደርስ ሲጥ አለች” ይባላል፡፡ “ጦም ጧሚና ሰው ጠባቂ” ሲባልም ሳትሰሙ አትቀሩም፡፡ ያልተነካካችሁ፣ የሰው ላብ፣ የሰው ደም፣ የሰው ሃቅ… የሀገርና የወገን ዕንባ… በእጃችሁ የሌለባችሁ ወገኖች ይበልጥ ተጠንቀቁ፡፡ በነፃነት ቀን የምናፍርበት መጥፎ ሥራ ይዘን እንዳንዋረድ አሁኑንና ከአሁኑ እውነተኛ ንስሃ እንግባ፡፡ ሀገራችን ስትፀዳ የሚወጣ ዕድፍና ቆሻሻ ይታየኛል፡፡ ከቤተ መንግሥት ተጠራርጎ የሚጣል እጅግ የሚገማና የሚሰነፍጥ ቆሻሻ ይታየኛል፡፡ ዲያቆናት፣ ደባትር፣ ካህናትና ጳጳሣት ከየቤተ ክርስቲያናት እንደቁንጫና ትኋን በፍሊት ተጠራርገው ሲወገዱና ዲያብሎስ በነሱ ውስጥ ሲወገር ይታየኛል፡፡ ቤተ እግዚአብሔርን መጫወቻና መሣቂያ መሣለቂያ እንዳደረጉት ሁሉ ማጣፊያው ለሚያጥራቸው መከራና ስቃይ ይዳረጋሉ፤ ያም ቀን ቀርቧል፡፡ በቤተ ክርስቲያናት አካባቢ የሚደረጉ ወንጀሎችንና ነውሮችን በሚመለከት ዝርዝሩን ብንናገር ቤተ ክርስቲያን የሚሄድን ሰው ተስፋ ማስቆረጥ ይሆናል፡፡ በጎቹን ቀበሮና ተኩላ የሚያስበላ እረኛ ዋጋውን ከጌታው ያገኛል፡፡
አዲስ አበባ የኦሮሞ ናት፡፡ ያን ማን ካደ? ከመነሻውስ አዲስ አበባን ስጡን ብሎ በሰላማዊ ሰልፍም ይሁን በወረቀት አቤቱታ ያቀረበ አለ ወይ? “ና አልመታህም!” አለው አሉ አንዱን፡፡ “ና አልመታህም”ን ምን አመጣው? አለና ሸሸው አሉ፡፡ እናስ! “አዲስ አበባን ለኦሮሞ ሰጠን፤ በኦሮምኛ የሚያስተምሩ ት/ቤቶች እንዲከፈቱ…” ቲሪሪም ቲሪሪምን ምን አመጣው? ወያኔዎች ጊዜ ካገኙ ገና ብዙ ይዘባርቃሉ፤ እንኳን ከፎከረ ከወረወረም የሚያድነው አምላከ ኢትዮጵያ ይሠውረን እንጂ ብዙና ብዙ የሚያጨራርሱን ዕቅዶች በመጋዘናቸው ውስጥ አሉ፡፡ በኦሮምኛ ይቅርና በጋፋትኛስ ቢሆን አንደኛ ትምህርት ቤት ቀርቶ ዩኒቨርስቲስ ቢሆን እንዳይከፍት የተከለከለ ወገን አለ ወይ? የምን ቅቤ አንጓችነት ነው? ማነው ሰጪ? ማንስ ነው ተቀባይ? ማን ነው መፅዋች? ማንስ ነው ተመፅዋች?
ኦሮሞዎችና አማሮች ስሙኝ፡፡ በልጅነቴ ልጆችን የምናጣለበትንና እኔም ሕጻን ሳለሁ እያጣሉኝ ትልልቆቹ የሚዝናኑብኝን አንድ ጨዋታ ላስታውሳችሁ፡፡ ጎርመስ ጎርመስ ያሉት ነፍስ ያላወቁ ትናንሽ ልጆችን ያመጡና በእጃቸው መዳፍ ላይ ምራቃቸውን እንትፍ ይላሉ፡፡ ከዚያም ወደ ሁለት ልጆች መሀል ይዘረጉና “የማን አባት ገደል ገባ፤ የማን አባት ገደል ገባ!” ይላሉ፡፡ አባቱ ገደል እንዳይገባበት በመሥጋት ቀድሞ “የጀገነው” ልጅ ያን ምራቅ በማበስ ለመቅደም ፈራ ተባ ይል የነበረውን ሌላውን ልጅ ይቀባዋል፡፡ ያ ተደፈርኩ ያለው ልጅ ምራቅ የቀባውን ልጅ በዱላ ማቅመስ ወይም  የባላንጣውን ወገብ በትግልመሰቅሰቅ ይጀምራል፡፡ ጠቡ እየከረረ ይሄዳል፡፡ ልጆቹ በእልህ ሲፋለሙ የጠቡ አነሳሾች አንድ ጥግ ጥላ ላይ ቁጭ ብለው እየተደሰቱ ይዝናናሉ – እንደወያኔ በሰው ስቃይ መደሰት፤ ዘመነ ግላዲያተር በሉት፡፡  በሰባና በሰማንያ ዕድሜ ውስጥ የሚገኙት እፍኝ የማይሞሉ ወያኔ ትግሬዎች በነዚህ ኆልቁ መሣፍርት በሌላቸው አማሮችና ኦሮሞዎች መሀል በሚፈጥሩት አርቲፊሺል ጠብ ሊዝናኑና ሂትለራዊ አገዛዛቸውን ሊቀጥሉ መሆኑን የማይረዳ ዜጋ ካለ በርግጥም በትንሹ የዋህ ነው፡፡ የተደገሰለትን የዕልቂት አታሞ በራሱ ጊዜ እየደለቀ ወደ መቀመቅ ለመውረድ የተዘጋጀ የለዬለት በግ ነው፡፡ መቶና ዘጠና ሚሊዮን በግ ደግሞ ሊኖር አይገባም፡፡ የእስካሁኑ ይብቃን፡፡ ለራሳችን ስንል ነው የሚበቃን ደግሞ፡፡
ስለዚህ የትኛውም ከተማ ለማንም ተሰጠ ይባል፤ ግዴለም፡፡ ኢትዮጵያም ከነነፍሷ ለጭዳነት ቀርባ ባወጣች እየተቸበቸበች አይደለም እንዴ ? በነዚህ ማፊያዎች ያልተሸጠ ነገር፣ በወያኔ ያልተጓጓዘ ነገር፣ ሕወሓት ያላደረሰው ጥፋት ከፀሐይ በታች ምን አለ? ስለዚህ ለማይቀረው ነፃነታችን ወደፊት ከሚገለጥልን አቅጣጫ የሚመጣውን መልካም ንፋስ ከመጠበቅና የበኩላችንን አስተዋፅዖ በምንችለው ከማበርከት ባለፈ በነዚህ ያበቃላቸው የሰይጣን ሽንቶች እንዳንታለል የዜግነቴን አደራ እላለሁ፡፡
ለመሆኑ የኦሮሞው ችግር የስም ለውጥና በራስ ቋንቋ መናገር አለመቻል ነው እንዴ? አለቃ ገ/ሃና ምን አሉ? “ይቺ ሌላ፣ ያቺ ሌላ!”  አዳማና ናዝሬት፣ ቢሾፍቱና ደብረ ዘይት፣ ፊንፊኔና አዲስ አበባ፣ ጂጂጋና ጂግጂጋ፣ አለማያና ሀሮማያ፣ አዋሳና ሀዋሳ፣….  በራሳቸው ዳቦ የሚያስገኙ ቢሆን፣ ዴሞክራሲና ነፃነት የሚያመጡ ቢሆን፣ ስደትን የሚያስቀሩ ቢሆን፣ በመቶዎች በረንዳ የሚያድሩ ዜጎቻችንን ቤት ውስጥ የሚያሳድሩ ቢሆን፣ የወያኔን የመሬት ዘረፋና የሕወሓታውያንን ጋጠወጥነት የሚከላከል ቢሆን፣ የኢትዮጵያን አንጡራ ሀብት ከሕወሓት ዘረፋና ንጥቂያ የሚታደግ … ቢሆን ኖሮ የኔም ስም ከምሕረት ወደ ሥምረት ቢለወጥ ግድ ባልነበረኝ፡፡ ግን ግን ከዚያች ሴተኛ አዳሪ የምንማረውና ልብ የምንገዛው መቼ ይሆን? እንደወያኔ ያለ ሞላጫ አጭበርባሪ በ“ነገ እሰጥሻሁ” የማያልቅ ነገ  እያታለለ ቢያሰለቻት ጊዜ “አጭበርባሪ ‹አይበልጠኝም›!” አለቻ! ቋንቋ የመግባቢያ መሣሪያ ሆኖ ሳለ ወያኔ ቤተ መንግሥት ውስጥ ቁጭ ብሎ ያሻውን እያደረገ በዚህ በጣም ትንሽ ነገር ያጨራርሰናል፤ ለነገሩ እነሱ ምን አጠፉ? ገልቱዎቹ እኛ! በ“ማን አባት ገደል ገባ!” የሕጻናት ጨዋታ ተሸንፈን ሀገራችንን ከኛ ላነሱ ደናቁርት የሰጠን እኛው ነንና there is no one to blame. ዓለማችን ውስጥ ከ7106 የማያንሱ ቋንቋዎች ይነገራሉ፡፡ አንዱ አንዱን ይውጣል፤ አንዱ ከአንዱ ማሕጸን ይወጣል፡፡ በዚህ ሰው ይተላለቃል? ወይ ሞኝነት! በጀመርኩት እንግሊዝኛ ባወራ፣ በኦሮምኛ ባወራ፣ በአማርኛ ባወራ፣ በትግርኛ ባወራ፣ በጉራግኛ ባወራ፣ በሱማሌኛ ባወራ፣… ሃሳቤን ገለጥኩበት፣ ከሰው ጋር ተገናኘሁበት እንጂ ቋንቋ እኔን ፈጠረኝ እንዴ? ኢንሻኣላህ – እመለስበታለሁ፡፡ ግን ልድገመው – የቀጣፊ ሲሳይ አንሁን!! ችግራችን የሀገር ማጣት እንጂ የቋንቋና የቦታ ስም አይደለም፡፡ ወያኔዎች ዳቢትና ወርቹን፣ ፍሪምባና ጭቅናውን ይዘው እኛን በባዶ ጭራና ለዋገምትና ለዋንጫ እንኳን በማይውል ጠማማ ቀንድ ሲያጣሉን ማየት እጅግ ያማል፤ እናንተንስ አያማችሁም? mz23602@gmail.com

የወገራ ገበሬዎች ላይ የታወጀው ፍጅት እና የእኛ ዝምታ source zehabesha

የወገራ ገበሬዎች
ከሙሉቀን ተስፋው
አገዛዙ በዐማራ ገበሬዎች ላይ ይፋ ጦርነት ካወጀ አንድ ዓመት ሆነው፡፡ በተለይ ደግሞ የወገራ ገበሬዎች ላይ ከባድ መሣሪያ ሳይተኮስ፣ የገበሬዎች ቤት ሳይቃጠል፣ ሰው ሳይሞት ሳምንት አይደፍንም፡፡ የትግሬው አገዛዝ በከባድ መሣሪያ ቤቶችን ሲያነድ፣ ሕጻናትንና አቅመ ደካሞችን ሲገደል እያየንና እየተመለከትን ምንም እያደረግን አይደለም፡፡ ጉዳዩ ዓለም አቀፍ ትኩረት እንኳ እንዲያገኝ እያደረግን አይደለም፡፡ በወገራ መንግሥትን ይጥላ፣ ይውደድ አገዛዙ ጉዳዩ አይደለም- በአካባቢው የተገኘ ዐማራ የሆነ ሁሉ እስካፍንጫው በታጠቀ የትግሬ ጦር ዒላማ ይደረጋል፡፡
በርካቶች ከቤታቸው ተፈናቅለዋል፤ ሕጻናት ከትምህርት ገበታቸው ተለይተዋል፡፡ የአባውራ ሴቶች ይደበደባሉ፡፡ ይህ የአለፉት ስምንት ወራት የወገራ ገበሬዎች ሁኔታ ነው፡፡ ይህችን ትንሽ ማስታዎሻ ስጽፍ እንኳ ሁለት ወንድማማቾች በከባድ መሣሪያ ወድቀዋል- የአባ ጋሻው ልጆች (መልካሙና አደራጀው)፡፡ የወገራ ገበሬዎችን አንድም ሳይለይ ነው አገዛዙ ጦርነት የከፈተባቸው፡፡
ከሁለት ቀናት በፊት በግብርናውም ሆነ በጉብዝናው የታወቀ አቶ ጓዴ ጌጡ የሚባል ወጣት ነበር፡፡ ሦስት የትግሬ ወታደሮች ከበቡት፡፡ ሦስቱንም አጋደማቸው፤ በመጨረሻ በትግሬ እጅ አልወድቅም ብሎ ራሱን ሰዋ፡፡ ገበሬው ያለበት ሁኔታ ይህ ነው፡፡ በየቀኑ ወደ አካባቢው የሚጨመረው ጦር ከሕዝብ ጋር ሳይሆን ከውጭ ወራሪ ኃይል ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው የሚመስለው፡፡
ስለ ወገራ ገበሬዎች ዝም ማለት የለብንም!! የሕዝባችን ዕልቂት ሊገደን ይገባል!!

በአፋን ኦሮሞ” አማካኝቶ ማስተር ፕላኑን በጓሮ በር – (ከኤርሚያስ ለገሠ) source zhabesha



ህውሃት ለሁለት የተሰነጠቀ ሰሞን ጐልተው ከታዩ ባህሪያት አንዱ የኦህዴድ ካድሬዎች “የኦሮሞ ብሔርተኝነት ” ካርድ የመዘዙበት ነበር። እነ ኩማ ደመቅሳ እና ግርማ ብሩን ጨምሮ በመዘዙት ካርድ “የትግራይ የበላይነት ሊውጠን ነው” በማለት ወደ ስልጣን ጫፍ ( ጠቅላይ ሚኒስትርነት ጨምሮ) ለመቆጣጠር የተጉበት ነበር።
እናም በእነ ግርማ ብሩ የተመራው ቡድን የኦሮሞ ብሔርተኝነት ይቀሰቅሳል ብሎ ያሰበውን እቅዶች በአጭር ጊዜ ውስጥ ይፋ አደረገ። ከእነዚህ ተግባራት አንዱ በአዲሳአባ የሚሰሩ ሥራዎች ተለይተው የቀረቡበት ነበር። ከስራዎቹም ውስጥ አንዱ ” በአዲሳአባ አምስት ዞኖች ውስጥ በሚገኙ 28 ወረዳዎች በአፋን ኦሮሞ የሚያስተምሩ 28 አንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች መክፈት” የሚል ነበር። በነገራችን ላይ በወቅቱ አዲሳአባ በአምስት ዞኖች እና 28 ወረዳዎች የተከፈለችበት ነበር።
እነዚህ ትምህርት ቤቶች ተገንብተው እስኪያልቁ አምስቱም ዞኖች በአጣዳፊነት ነባር ትምህርት ቤቶችን በመለየት ለጐልማሶች የማታ፣ ለህጻናት እና ታዳጊዎች የቅዳሜ እና እሁድ እንዲሁም በክረምት ኢ_መደበኛ ትምህርት እንዲጀመር ጥብቅ ኦህዴዳዊ ትእዛዝ ተላለፈ። በድርጅት ቋንቋ መደብ ወረደ። መደቡን ለማስፈፀም ደግሞ የአዲሳአባ ካቢኔ የነበሩት ሊቀመንበር አሊ አብዶ ፣ ሀይሉ ደቻሳ ፣ ወ/ሮ ስመኝ ውቤ( የአፈ ጉባኤ ደግፌ ቡላ ባለቤት እና በኋላ ላይ በአዜብ መስፍን ከም/ል ሚኒስትርነት የተባረረች የምንወዳት እህታችን) እና አምባሳደር ሰለሞን ተመደቡ። ተግባሩ በቁልፍ ደረጃ በመቀመጡ ስራውን ያንጠባጠበ ካድሬ በኦህዴድነት መቀጠል እንደማይችል ተገለፀ።
በየቀበሌው የሚገኝ ካድሬ ቤት ለቤት እያሰሰ የኦሮሞ ዘር አለው የሚለውን አዲስአበቤ እንዲመዘግብ አደረገ። እንደ መሰረተ ትምህርት ዘመቻ ፍቃደኛ ያልሆነውን ማስገደድ ተጀመረ። በደርግ ጊዜ ዝነኛው ቆምጬ አምባው ” አስኳላ የማይሄድ ቡዳ ነው!” ያለውን በተሞክሮ በመውሰድ የአዲሳአባ ኦህዴድ ካድሬዎች ” አፋን ኦሮሞ የማይማር የነፍጠኛ ተላላኪ ነው!” የሚል ማዕከላዊ መልእክት ቀርፀው በጥቅም ላይ አዋሉ።
ስራው በተጀመረ የመጀመሪያው ወር የተመረጡት አምስት ትምህርት ቤቶች በምሽቱ ክፍለ ጊዜ ከጠቅላላው አዲሳአባ በአማካይ 500 ተማሪ ተገኘ። ቅዳሜ እና እሁድ በተዘጋጀው የህጻናት፣ ታዳጊዎች እና ወጣቶች ክፍለጊዜ በአማካይ አንድ ሺህ የሚጠጋ ተገኙ። የኦህዴድ አብዮታዊ ካድሬዎች አጀማመሩ ጥሩ እንደሆነ ገመገሙ።
ስራው በተጀመረ ሶስተኛው ወር የምሽቱ 60 ፣ የሰንበቱ ወደ 90 ተማሪ ብቻ ቀረ። አምስቱ ትምህርት ቤት ታጥፈው በዞን ሁለት ውስጥ ወደ ሚገኘው ተግባረ እድ ትምህርት ቤት እንዲጠቃለል ተደረገ። በአራተኛው ወር እንደ ኮንደሚኒየም ወደ 40/60 ተቀየረ። አካሄዱ አስደንጋጭ የሆነበት ኦህዴድ ” ሁሉም ዜሮ ዜሮ” መመዝገቡ በፊት ትምህርቱ ባልተገለፀ መመሪያ እንዲቀር ተወሰነ።
ከሁሉም የሚገርመው ነገር አዲሳባ የሚኖር አንድም የኦህዴድ ባለሥልጣን ልጆቹን አፋን ኦሮሞ እንዲማሩለት አልሰደደም። በክረምቱ ክፍለጊዜም ሆነ በሰንበት ባለሥልጣናት ልጆቻቸውን የሚልኩት የእንግሊዘኛ እውቀታቸውን የሚሳድጉበት ከ3ሺህ ብር በላይ የሚከፈልባቸው ውድ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ትምህርት ቤቶች ነበር። አንዳንዶቹ ከቋንቋው በተጨማሪ ልጆቻቸው እንዲዝናኑ የሚልኩት ወደ ትውልድ ገጠሪቱ ኢትዮጵያ ሳይሆን ወደ ሰሜን አሜሪካ እና አውሮፓ ነበር ። አሁንም የተቀየረ ነገር ያለ አይመስለኝም። እንደውም እየሰማን ያለነው በሌብነት እና መሬት ችብቸባ ኪሳቸው ያበጠ የኦሮሚያ ዞን እና ወረዳ ካድሬዎች ልጆቻቸውን የሚያስተምሩት አዲሳባ ቤት ተከራይተው እጅግ በጣም ውድ በሆነ ” ከእንግሊዘኛ ውጭ መናገር ክልክል ነው!” የሚል ማስታወቂያ የተለጠፈበት ትምህርት ቤት እንደሆነ ነው። ተወደደም ተጠላ መሬት ላይ ያለው እውነታ ይሄ ነው።
ከአዲስአባ አወቃቀር አኳያም የተቀየረ ነገር የለም። አዲስአበቤ እንኳን በሕውኃት ድርጅታዊ መመሪያ የተላከለትን ቀርቶ ሌላውንም ቢሆን በጥሞና የሚመለከት አስተዋይ ህዝብ ነው። (” ወርቅ ህዝብ ነው!” ብዬ ልገልፅ ነበር፣ ኩረጃ ይመስልብኛል ብዬ ተውለኩት።) ያለማጋነን አዲስአበቤ የህውሓትን አካሄድ እና አላማ ከመገንዘብና ከመታገል አኳያ የቀደመው የለም።
እናም ዛሬ ” የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ” በሚለው አባይ ፀሐዬና በረከት ስምኦን የፃፈው አዋጅ ላይ ” አስተዳደሩ በአፋን ኦሮሞ ልጆቻቸውን ማስተማር ለሚፈልጉ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ማደራጀት አለበት” የሚል ተፅፎ ስመለከት የተሰማኝ ከላይ የተገለጠው ነው። እነ አባይ በዚህ አዋጅ አማኸኝተው ማስተር ፕላኑን በጓሮ በር ማስገባታቸው እንዳይታወቅ “የዶሮን ሲያታልሏት” ማታለያ ይዘው ብቅ ማለታቸው እርስ በራስ ለማጋጨት ነው። ሌሎች የህጉ እሳቤዎች መሰረታዊ ምንጫቸው ይሄ እና ይሄ ብቻ ነው።

Wednesday, June 28, 2017

ሌ/ጄነራል ጻድቃን ፣ ህወሃት ፣ ኤርትራ እና ቀይ ባህር source zehabesha

በነጻነት ቡልቶ
ክፍል አንድ
ጄነራል ጻድቃን፣ “የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፓሊሲ” እና  “የፓለቲካ ችግሮች
በግሪክ አቴናና በስፓርታ መካከል የተካሄደውን የጦርነት ታሪክና ከጦርነቱ ጋር የተያያዙ ስትራቴጃካዊ ጽንሰ ሃሳቦች በማፍለቅ ከሚደነቀው ጥንታዊው የታሪክ ጸሃፊ  የቱስዳይስ  The Peloponnesian war  ጀምሮ  እስከ  የጀርመኑ ካርል ቮን ክልሽዊትዝ  On War ፣  የባህር ሃይል  ስትራቲጂ አባት አልፌሬድ ማሃን The influence of Sea Power Upon History፡ ከዘመን ተሻጋሪ  የስትራቴጂ አስተምሮዎች ፈላስፋ ቻይናዊው ከሰን ዡ The Art of War  አንስቶ እሰከ ሉትዋርክ፣ ኮሊንስ የመሳሰሉ የዘመናችን የስትራቴጂና የደህንነት ጥናቶች ታላላቅ ተመራማሪዎችና  ምሁራን  የጻፏቸውንና ያፈለቁዋቸውን የስትራቴጂ ጽንሰ ሃስቦችና ቀመሮች  በጥልቀት ማጥናትና ማወቅ አስፈላጊና ጠቃሚ ናቸው፡፡  የሴኪዩሪቲና የስትራቴጂ እውቀቶችን ባካበቱ ምሁራንና ተመራማሪዎች የሚጻፉ የአብይ ስትራቴጂ (Grand strategy) ንድፈ  ሃሳቦችና ጽንሰ ሃሳቦች፣  ከነዚህ የሚመነጩ የብሄራዊ ደህንነት ስትራቴጂ ቀመሮችን ተመርኩዞ  የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፓሊሲዎችን መንደፍ ሀገራችን ኢትዮጵያ ለተጋረጡባት ድርብርብ የፖለቲካ ችግሮችና ከችግሮቹም የሚመነጩትን ዘርፈ ብዙ የደህንነት አደጋዎችን ለመከላከል የማይናቅ ድርሻ አላቸው። በእነዚህም ዙሪያ  ጥልቀት ያላቸው ጥናቶችን ማድረጉ አስፈላጊ ነው። እነዚህንም የሚያስፈጽሙ አካላት መኖርና መጠናከር ለኢትዮጵያም ሆነ ለማንም ሀገር አስፈላጊ ከሆኑ ተቋማት ውስጥ በቀዳሚነት የሚቀመጡ መሆናቸው አይካድም። ከዚህ አኳያ ጄነራል ጻድቃን በእውቀት ላይ የተመሰረቱ ፖሊሲዎችና ተቋማት ለአንድ ሃገር የሚበጁ እንደሆኑ ወደ አደባባይ ጉዳዩን ማቅረባቸው ያስመሰግናቸዋል።
ነገር ግን በዋነኝነት በአንድ ሀገር ውስጥ የሚገኙ የፖለቲካ ስርአት መሪዎች ባህሪ ፣ የፖለቲካ ታሪካቸው (track record)፣ የሚከተሉት ኣካሄድና የፓለቲካ ፍላጎት በሀገሪቱ ዕጣ ፈንታ ላይ ቀዳሚና  ወሳኝ (Decisive) ድርሻ እንዳላቸው ክርክር የሚያስፈልገው ጉዳይ አይደለም። ይህንን ቀላል ዕውነት መረዳት የችግሮቻችንን መሰረት ለማወቅ ፣ አውቆም በቀዳሚነት የሚያስፈልገው ያለፈው 26 አመት ህወሃት የዘረጋውን  የፓለቲካ ስርአትና ተከትሎት የመጣውን  ግዙፍ  የደህንነት አደጋዎች ለመገንዘብ ይረዳናል።  ይህን አደጋ ለመቀልበስ ደግሞ ቁርጠኝነትና  የፓለቲካ ወኔ (Political will)  መኖር   ዋናው ቁልፍ ነው። ይህም በመሆኑ ነው “የፓሊሲዎች ቈንጮ የሆነውን የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፖሊሲ” በባለቤትነት፣ በአስፈጻሚነትና በኣስተግባሪነት አሁን ላለው የሀገሪቱ የደህንነት ስጋት ዋና ቀፍቃፊ ምንጭ ለሆነው  የሕወሃት አመራር መስጠት ውሻን ሉካንዳ ቤት እንዲጠብቅ ከማድረግ ይቆጠራል ብዬ የምከራከረው። የብሄራዊ  ደህንነት አደጋዎች አመንጪና አሽከርካሪ (driver) የሆነውን አካል የዚህ ፖሊሲ ባለቤትና አስፈጻሚ ማድረጉ ስርአቱን ትንሽ ጠጋግኖ ለማስቀጠል ይረዳ እንደሆን እንጂ በዘለቄታው የኢትዮጵያን የደህንነትና ተያያዥነት ያላቸውን ዘርፈ ብዙ የፖለቲካ  ችግሮች  ማስወገድ አይቻልም። እንዳውም በተቃራኒው እነዚህ  ዘርፈ ብዙ የሀገሪቱ የፓለቲካ ችግሮች ተወሳስበው መቀጠላቸውና  ሀገሪቱንም ሆነ የአፍሪካ ቀንድን ለከፋ ትርምስና የደህንነት ኣደጋ ማጋለጣቸው አይቀሬ ነው።
ህወሃት የስልጣን ዕድሜውን ማስቀጠያ መርህ ወይም ከልቡ የሚያምንበት ገዢ ሃሳብ ከጠፋበት ሰንበትበት ብሏል። ህወሃቶችንና ኢህአዴጎችን አጣብቆ የሚያቆያቸው መርህ ፍርክርክ ባለበት፤ በተለይ ከቀድሞ መሪያቸው ከመለስ ዜናዊ ህልፈት በኋላ በእውር ድንብር በሚሄዱበት፤ በውስጣቸው የሚገኘው ቅራኔና ክፍፍል በጦዘበት፤ ሆኖም ላንሰራፉት የአንድ ብሄር የበላይነትና የዘረፋ ስርአት መሳሪያ የሆነን የመንግስት ስልጣን እንዳያጡ ተጣብቀው የሚገኙበት ሁኔታ ላይ ነው ያሉት። የኢትዮጵያን ህዝብ የሚያማልሉበት፣ የሚያሳምኑበትና ከጎናቸው የሚያሰልፉበት ሃሳብ እንደሌላቸውም ግልጽ ከሆነ ቆይቷል። ባጠቃላይም በህወሃት የበላይነት ስር የሚገኘው የፖለቲካ ስርኣት የቅቡልነት፣ የህጋዊነት፣ ብሎም የራስ መተማመንና የውህድ አመራር እጦት ድርብርብ ቀውሶች ታማሚ ሆኖ በሚማቅቅበት በአሁኑ ቀውጢ ሰዓት ላይ ጄ/ል ጻድቃን አንድ መላ ይዞላቸው የመጣ ይመስላል።  ምናልባትም “የሕዝብ የአስተሳስብ አንድነት” ሊያመጣ የሚችል ሁሉን አሰባሳቢ ገዢ ሃሳብ ነው ብለው ገምግመው ሊሆን እንደሚችል ከግምት ውስጥም ማስገባት ያስፈልጋል።
“ከህገ መንግስቱ በታች የፓሊሲዎች ቁንጮ” የሆነው የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፓሊሲ በአግባቡ ተቀርጾ፣ ይህንን በቋሚነት የሚሰራ ኣስፈጻሚ አካል ማደራጀት ዋነኛ የኢትዮጵያ የፓለቲካ ችግሮች መፍቻ ምትሃታዊ አቅም (ማጂክ ዋንድ) ወይም የብር ጥይት (ሲልቨር ቡሌት) እንዳለው ተደርጎ በጄነራሉ ሰፊ ትንታኔ የተሰጠበት አይነተኛ ምክንያትም ከላይ የተዘረዘሩትን ግቦች ለማስፈጽም እንዲረዳ ታስቦ ሊሆን ይችላል። በመሰረቱ የኢትዮጵያ ዋነኛ ችግር ራሱ የህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ ነው። አገዛዙ የሚያራምዳቸው ዘርፈ ብዙ ጸረ-ህዝብና ጸረ -ዲሞክራሲያዊ ተግባሮቹ  በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙ ችግሮች ዋነኛ ምንጭና ተዋናይ መሆኑን በገሃድ የሚያሳዩ ምስክሮች ናቸው። ለዚህም ነው ጄ/ል ጻድቃን በሰፊው ትንታኔ የሰጠበት የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፓሊሲ መኖር አለመኖር ወይም ይህን ፓሊሲ የሚከታተልና አማራጭ ሃሳቦችን የሚያቀርብ ቋሚ አካል መኖር አለመኖር ሕወሃትን ቀስፎ ከያዘውና ከሚያሰቃየው የውስጥ ደዌው ጋር እምብዛም ተያያዥነት የለውም ብሎ መከራከር የሚቻለው። ጄ/ል ጻድቃን “የፓለቲካ ችግሮች”  በሚል ጥቅል ሀረግ አደባብስው ያለፉዋቸውን ሕወሃት ሰራሽ የሆኑ ችግሮችን እንደሚከተለው ማቅረብ ይቻላል።
ዋናው የኢትዮጵያ የደህንነት ኣደጋ የሀቀኛ ዴሞክራሲያዊ ስርአት አለመኖር ነው። ትልቁ የደህንነት አደጋ የኢትዮጵያን የብሄር ችግሮች ፈትቷል ተብሎ ከጅምሩ ሕወሃት እንደ ትልቅ ስኬት ሲመጻደቅበት የቆየው ፌዴሬላዊ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ዴሞክራሲያዊም ፌዴራላዊም አለመሆኑ ነው! የህወሃትን ፍላጎት፣ የበላይነት፣ የዘረፋ፣ የኣድሎአዊነትና የዘረኝነትን ስርዓት ማስጠበቂያና ማስቀጠያ መሳሪያና ጭንብል ከመሆን በዘለለ የተባለውን ሐቀኛ ዴሞክራሲንም ሆነ ፌዴራሊዝምን እውን አለማድረጋቸው ነው።
ህወሃት መራሹ የኢትዮጵ እገዛዝ ዛሬ የኢትዮጵያን ህዝብ በባርነት ቀንበር ውስጥ ጠፍንጎ ይዞ፣ ስልጣን ከላይ እስከ ታች ድረስ በአንድ ብሔር ቁጥጥር ስር አስገብቶ አይን ያወጣ ዘረፋ፣ ግድያና አፈና መፈጸሙና ማስፈጸሙ የህዝብና የዜጎች የዕለት ተዕለት ትእይንት የሆነባት አገር ናት ኢትዮጲያ!  ህዝቦቿ ባዶ እጃቸውን አደባባይ ወጥተው የመብትና የዴሞክራሲን ጥያቄ ባቀረቡ ቁጥር መልሳቸው በአጋዚ ቅልብ ጦርና በፌዴራል ፖሊስ  እንደ ጠላት በጥይት የሚቆሉባት፣ ዜጎቿ በጅምላ የሚታሰሩባት፣ የሚፈናቀሉባት፣ በየአመቱ በ10 ሚሊዮን የሚቆጠሩ ልጆቿ የሚራቡባት፣ በሺዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ለተሻለ ሕይወት ወደ ስደት ሲሄዱ በባሕር ላይ የዓሳ ነባሪ ቀለብ ሆነው የቀሩባት፣ እህቶቻችን የአረብ ገረዶች ሆነው ለወሲብ ጥቃት የተጋለጡባት፣ ከፎቅ ላይ እየተወረወሩና በፈላ ውሃ እየተቀቀሉ በየቀኑ ሬሳቸው ወደ አገር ቤት የሚጫንባት፣ ነዋሪዎቿ በቆሻሻ ክምር ናዳ የሚያልቁባት አገር ሆናለች ኢትዮጲያ!  ከዚህም በተጨማሪ ዜጎች የመኖር ዋስትና ተነፍጓቸው በሰላም ከቤታቸው ወጥተው በሰላም መግባት የሚችሉበት ሕይወት የሩቅ ዘመን ትዝታ ከሆነ ሰነባብቷል።  እንደ አሸን የፈሉ የስርዓቱ ሰላዮች እስከ ቤተክርስቲያንና መስጊድ ድረስ ሳይቀር ለመሰለልና አለመተማመንን ለመፍጠር  የተሰማሩባት፣ ዘረፋ፣ ውሸት፣ ሌብነትና ማጭበርበር ባህል የሆነበትና ሰዎችን እንደሸቀጥ የማዘዋወር ንግድ እየተንሰራፋ የመጣበት አስደንጋጭ ሁኔታም ተፈጥሯል። እነዚህና ሌሎች እዚህ ላይ ያልተዘረዘሩ ተወራራሽ ችግሮች ህወሃት በሚመራው አገዛዝ የተፈጠሩ ናቸው።
ጄነራል ጻድቃን በእድገትም፣ በዲፕሎማሲም ሆነ በሰላም ማስከበር ወዘተ በአለም ማህበረሰብ ዘንድ የሃገራችን ተቀባይነት ጨምሯል በማለት የህወሃትን አገዛዝ “ስኬቶች” እውቅና በመስጠት ችግሩ በዋነኛነት የውጪና የደህንነት ፖሊሲ ችግር ነው በሚል አገላለጽ  ለማድበስበስ ሞክረዋል። እንዲሁም ብጥብጥና ትርምስ የፈጠሩት የጸረ ሰላም ሃይሎች በቀጥታ ከሻዕቢያ ወይም በሻዕቢያ መንግስት አቀነባባሪነት የተፈጠረ ነው የሚል አንደምታ ያለውም ሃሳብ አስቀምጠዋል። በተለይም ደግሞ ጄነራሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ያነሳውን ተደጋጋሚ የመብትና የነጻነት ጥያቄ በሻዕቢያ ተላላኪነት የፈረጇቸው ሽብርተኞችና የጸረ ህዝብ ሃይሎች ሴራ አድርገው ለማቅረብ የሞከሩበት ሂደት በጣም አስገራሚ ነው።
የህወሃት ትግራዮች የበላይነት በሌሎች ህዝቦች ኪሳራ በኢኮኖሚ፣ በፓለቲካ፣ በወታደራዊ፣ በደህንነት ተቋማት ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ እንዲኖራቸው መደረጉና ይህም ኢፍትሃዊ አሰራር በሌላው ኢትዮጵያዊ ላይ የፈጠረው የበይ ተመልካችነት፣ የባይተዋርነትና የሁለተኛ ደረጃ ዜግነት ስሜት በህዝቦች አብሮ የመኖር እድል ላይ አሉታዊ ጥላውን አሳርፏል። ይህም ጤናማና የተረጋጋ ማህበረሰብ ለዘለቄታው ለመፍጠር በሚደረገው ሂደት ላይ የራሱን ሳንካ ማሳረፍ ብቻ ሳይሆን ህዝብ ለህዝብ፣ ብሄር ለብሄር በጎሪጥ ኣንዲተያይ፣ በተቃርኖ እንዲቆምና ወደ ግጭት ምናልባትም ፍጅት ወደሚያስከትል ደረጃ ያደርሰው እንደሁ እንጂ  የብሄራዊ ደህንነትን ወደሚያረጋግጥ፣ የሰላምና መረጋጋትን ዋስትና ወደሚያስቀጥል መንገድ ፈፅሞ ሊመራው አይችልም።
እጅግ ጥልቀት ያለው የደህንነት ፖሊሲ ተቀመረ አልተቀመረ ፋይዳ ቢስ ነው። መሰረታዊ ምክንያቱም ይህ ፓሊሲ ሊከላከላቸው የሚችሉ የደህንነት አደጋዎች መሰረታዊ ምንጫቸው የደህንነት ፖሊሲ አወጣለሁ የሚለው ራሱ ህወሃት የዘረጋው አምባገነናዊ፣ ዘራፊ፣ ዘረኛ፣ አድሎአዊ የአፓርታይድ መሰል ስርአት በመሆኑ ነው! ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል እንዲሉ ህወሃት ራሱ የሃገሪቱ ዋነኛ የደህንነት ስጋት ሆኖ ሳለ “በጥልቀት የተጠናና ምልእኡ የሆነ የሃገሪቷን የደህንነት ፖሊሲ አስፈጻሚ/አስተግባሪ ምሆኑ በጣም አስቂኝ ያደርገዋል። ጄነራሉም ቢሆኑ ህወሃትን የሃገሪቷ የደህንነት ስጋቶችና አደጋዎች የሚያመንጭ ኃይል ሆኖ ሳለ ራሱ መፍትሄ ብሎ የሚያስቀምጠውን የደህንነት ፖሊሲ ባለቤትና አስፈጻሚ ሊሆን እንደማይችል መረዳት የገባዋል። በህወሃት የበላይነት የሚዘወረው አገዛዝ የሃገሪቷ ትልቁ የደህንነት ስጋትንና አደጋ ስለመሆኑ መካካድ አያስፈልግም። ጄነራል ጻድቃን ይህንን ሐቅ ጠንቅቀው የሚረዱት ይመስለኛል።
ከላይ እንደተጠቀሰው እጅግ ከባዱ የኢትዮጵያ የደህንነት አደጋ ህወሃት በመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ያንሰራፈው የትግራይ የበላይነት ወይንም የገዢ መደብነት ስርአት ነው። ይህም ስርዓት በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በመንግስታዊ ተቋማት፣ በመከላከያ፡ በደህንነት  “እንወክለዋለን የሚሉትን” የትግራይ የህዝብ ቁጥር ፈጽሞ የማይመጣጠን የአናሳ ብሔር አባላትን የተጠቃሚነት፣ የፈላጭ ቆራጭነት፣ ኢፍትሀዊ በሆኑ መንገዶች ለዘመድ አዝማዶቻቸው ሁሉ ሳይሰሩ በአንድ ጀንበር ባለሃብት የሚሆኑበትንና የሚከብሩበትን መንገድ በግልጽና በስውር ያመቻቸ እኩይ ስርዓት ነው። በሌላ በኩልም  በየእስር ቤቶቹ የሌሎች ብሄር ተወላጆች “አንተ አማራ፣ አንተ ኦሮሞ፣ አንተ  ጉራጌ. ሽንታም ” በማለት እያዋረዱ ትግሪኛ ተናጋሪ በሆኑ የሰርዓቱ ሰዎች የሚፈጸሙ እጅግ ዘግናኝ ግፎችና ሰቆቃዎችን እዚህ መዘርዘሩ ለቀባሪው ማርዳት ነው። የዚህ መጥፎ ስርዓት ሰላባ የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሃያ ስድስት ዓመታት ያየው፣ የሰማው፣ የደረሰበትና ያንገፈገፈው የግፍ ዋንጫ ነውና! በብዙ መገለጫዎች የሕወሃትን የበላይነት፣ መሰሪነት፣ ስግብግብነት፣ ጭካኔ ማሳየት ይቻላል። ለዚህም ነው ህወሃት የሚዘውረው አገዛዝ ከመቼውም ጊዜ በላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ የደህንነት ስጋትና አደጋ ተደርጎ የሚቆጠረው። ጄነራል ጻድቃን ይህን ራሱ ስጋት የሆነውን ሃይል ነው እንግዲህ ሃገሪቷን የሚያረጋጋና ከተደቀኑባት የደህንነት አደጋዎችም መጠበቅ የሚያስችል የደህንነት ፖሊሲ እንደሚያወጣና የፖሊሲው ይዘትም ምን መሆን እንዳለበት የተናገሩት!
የኢትዮጵያ ህዝብ በፍትህ ህይወቱን የሚመራበትን፣ የህግ የበላይነት በሰፈነበት ስርአት የሚዳኝበትን፣ ፍትሃዊ የሆነ የስልጣንና የሐብት ክፍፍል፣ ማህበራዊ ፍትህ  የሚሰፍንበትን ስርዓት ከምንም ጊዜውም በላይ ይናፍቃል። ዜጎች በነጻነት አብረው የሚኖሩባት ፣ የዘላቂ ሰላምና ደህንነት ዋስትና የተረጋገጠባት፣ ብዙሃኑ እየተራበ ጥቂቶች በጥጋብ የማያገሱባት፣ ማሕበራዊ ፍትህና ብልጽግና ለሁሉም አካባቢዎች በተግባር የሚተረጎምባትን ኢትዮጲያን ማየት ይመኛል። ሆኖም ከምኞት ባሻገር ለነኚህ የተቀደሱ ዓላማዎች መሳካት ዜጎች ሁሉ ከልብ ሊጨነቁባቸው፣ ብሎም በጽናት ሊታገሉላቸው የሚገቡ ግቦች መሆን አለባቸው። አሁንም እደግመዋለሁ!   ዛሬ  በኢትዮጳያ  ውስጥ የተንሰራፋው የሕወሃት ገዢ መደብ ሁሉንም በባለቤትነትንና በበላይነት  ይዞ በሚገኝበት እጅግ አስፈሪና አሳፋሪ ሁኔታ ውስጥ እንገኛለን።
ይህ ዐይን ያወጣ አድሎአዊና ኢፍትሀዊ የስልጣን፣ የሀብትና የጥቅም ክፍፍል ብሎም ይህ ክፍፍል የፈጠረው አስከፊ የሆነ ብሄሮች የጎሪጥ የሚተያዩበት ሁኔታ ሊካድ አይገባውም። እንደውም የብልህና አርቆ አሳቢ፣ ዘመን ተሻጋሪ፣ ባለራይና  የፓለቲካ መፍትሄ አመንጪነት መነሻ መሆን ያለበት ይህን መራር ሐቅ ከምንም በፊት አስቀድሞ በመቀበልና በመጋፈጥ መሆን ይኖርበታል።፡ ምክንያቱም ይህ ነባራዊ   ሁኔታ ለዘለቄታው የሕዝብ አብሮ መኖር፣ ሰላም፣ መረጋጋትና ባጠቃላይ ለሀገሪቱ ህልውና የሚያሰጋ ትልቁ  የደህንነት ፈተና  በመሆኑ ነው። እናም ይህንን  አደገኛ አካሄድ በትዕግስት፣ በጥበብና በቁርጠኝነት በመቀልበስ  የአገሪቱን ህልውና፣ የሕዝቦችን  በእኩልነትና በሰላም መኖር ለማረጋገጥ መጨነቅና መታገል ሲገባ ነው እንጂ ጄነራሉ እንዳነሱት ሃሳብ የችግሮቹን ዋና ምንጭ ትተው ጉዳዩን ከውጪና ደህንነት ፖሊሲ ጋር  በዋነኘት በማያያዝ አይደለም።አለባበሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ እንዳይሆን።
በኢትዮጵያ ውስጥ መጥቶ የነበረው የጸጥታ ችግር አስቀድሞ ሊታይ ይችል ነበር። በሰው ህይወት፣ በንብረት ላይ ጉዳት ሳያስከፍል፣ የጊዜአዊ ኣስቸኳይ ኣዋጅ ሳያስፈልግ ለመከላከል ይቻል ነበር። ሀገር ተናውጦ “በጊዜያዊ አስቸኳይ አዋጅ ነው የቆመው” ይላሉ ጄ/ል ጻድቃን!  እውን የመጣው የህዝብ ቁጣና አልገዛም ባይነት የፖሊሲ አለመኖር ወይንስ የሕወሃት/ኢህአዴግ ፖሊሲዎች ጸረ-ህዝብነት ያመጡት ነው ብሎ ለጠየቀ ሰው መልሱ ግልጽና ግልጽ ሆኖ ይታየዋል። በተለያዩ ጊዜያት የተተገበሩ የህወሃት ፓሊሲዎች ያመጡት ድርብርብ ችግሮች መሰረቱ የስርዓቱ ጸረ- ዲሞክራሲያዊና ጸረ- ህዝብነት መሆኑ ላይ ነው። ሌላ ምንም ሚስጥር የለውም! ይህን መሰረታዊ ችግር በደህንነት ፖሊሲ ምሉዕነትና አፈጻጸም ያለመኖር  የመጣ ችግር ነው ብሎ ለማቅረብ መሞከር ሃገሪቱ አሁን የገባችበትን ቅርቃር በሚገባ ባለመገንዘብ ወይንም ኃላፊነት በጎደለው መንፈስ ሆነ ተብሎ ለራስ በሚሰላ ጥቅም አማካኝነት ችላ የማለት ጉዳይ እንደሆነ ተደርጎ ነው የሚወሰደው።
ጄ/ል ጻድቃን የስርዓቱን ዝቅጠት “የውስጥ የፓለቲካ ችግር” ሲሉ በደምሳሳው ቢገልጹትም የሀገሪቱን የፓለቲካ ችግሮች ዋና ዋና ገጽታዎች ከዚህ በፊት በጻፉት ጽሁፍ በስሱም ቢሆን እንደገለጹት በዚህኛው ቃለ ምልልሳቸው ሊገልጹና ሊዘረዝሩ አልደፈሩም። መሰረታዊ የህዝብ ጥያቄዎችና ከላይ የተዘረዘሩት እውነታዎች የሚቀየሩበት መሰረታዊ ለውጦች እስካልመጡ ድረስ “የህዝብ የአስተሳሰብ አንድነት” ሊመጣ ከቶም አይችልም። በሀገሪቱ የሚገኙ ችግሮች ስርአቱ የወለዳቸውና ያሳደጋቸው እንደመሆናቸው መጠን በዚህ ስርአት የህዝብ ጥያቄዎች መልስ ሊያገኙ እንደማይችሉ ያለፉት ሃያ ስድስት አመታት ስለ ስርአቱ ማንነትና ምንነት ብዙ አሳይቶናል፤ ብዙም አስተምሮናል። በዚህ ረዥም ሂደት ውስጥ ህወሃት ይበልጥ ከህዝቡ እየተነጠለ ዛሬ አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ የስርአቱን መውደቅ የሚናፍቅበት ሁኔታ ውስጥ ይገኛል። ህወሃት የህዝቡን የአስተሳሰብ አድማስ ወደ ሚፈልገው አቅጣጫ ለመምራት ቀርቶ የራሱንም ህልውና ለማቆየት ከማይችልበት አዘቅት ውስጥ መግባቱን ለማሳየት  ብዙ መድከም የሚያስፈልግ አይመስለኝም። እንዳውም ዋናው ጥያቄ መሆን ያለበት ““ሕወሃት የወደቀበት አዘቅት ውስጥ ምን ያህል ጊዜ በሕይወት ይቆይ ይሆን?” የሚለው ይመስለኛል።
በመቀጠልም አሁንም ትልቅ የደህንነት አደጋ  “እያረገዘ ያለ ሊኖር ይችላል” ይላሉ ጄ/ል ጻድቃን። የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ እነዚህ የተረገዙ ችግሮች የፖለቲካ ስርዓቱ መሰረታዊ ለውጥ እስካላመጣ ድረስ መፈንዳታቸው አይቀሬ ነው። ለማርቀቅና ለማጸደቅ ውይንም ለማሻሻል እያሰቡት ያለው የደህንነት ፓሊሲ ይህን የለውጥ ሱናሜ ሊያቆመው ከቶም አይቻለውም። ሌሎች የስርአቱ ፓሊሲዎች ሁሉ የሚመነጩት ከዚህ የህወሃት መለያ ከሆኑት ስግብግብነቱ፣ ጸረ ዲሞክራሲያዊና ጸረ ህዝብ ባህሪያቶቹ በመሆኑ ነው።”መከለስ ያለበት” የውጪና የደህንነት ፖሊሲም ከህወሃት ጸረ ህዝባዊነትና ጸረ ዲሞክራሲያዊነት የሚመነጭና የስርአቱን እድሜ ለማራዘም ተብሎ የሚቀመር በመሆኑ ከመነሻው ጄነራል ጻድቃን እንደተመኙት የችግሮቹ መፍትሄ ሆኖ ሊመጣ አይችልም።
መሰረታዊ የህዝብ ጥያቄዎች በመሰረታዊ ለውጦች እስካልተመለሱ ድረስም “የህዝብ የአስተሳሰብ አንድነት” ሊመጣ አይችልም። የሀገሪቱን ዘርፈ ብዙ የፓለቲካ ችግሮች ለመፍታት የማይፈልግ፣ ይህን ካደረግኩ ስልጣኔን አጣለሁ በሚል ስሌት ዘረኛና አምባገነን የሆነውን የህወሃት የፓለቲካና ኢኮኖሚያዊ የበላይነት ለማስቀጠል የሚተጋ፣ በተንኮልና በመሰሪነት እንዲሁም በጭካኔው የተካነ መሆኑ የተረጋገጠለት ስርዓት የአገሪቱን የጸጥታና የደህንነት ችግሮች ለዘለቄታው ሊፈታ የሚችል ሃይል ሊሆን አይችልም።ከገለማ እንቁላል ጤናማ ጫጩት አይፈለፈልም እንዲሉ! ራሱ የሃገሪቷ የደህንነት ስጋት ስለሆነ ከማንም በላይ የችግሮቹ ምንጭና መንስኤ ነው!
አርበኞች ግንቦት 7ም ሆነ ኦነግ እንዲሁም ሌሎች ጄ/ሉ ያልጠቀሷቸው ሃይሎች ህልውና መሰረት በሃገር ውስጥ ህወሃት የፈጠራቸው ሁኔታዎች፣ ጸረ ህዝብነቱና ጸረ ዴሞክራሲያዊነቱ፣ ራሱ ያወጣውን ህገ-መንግስታዊ መብቶች በተደጋጋሚ በመርገጥ ስላማዊ ህጋዊ ትግልን ለማድረግ ፈጽሞ በማይቻልበት ደረጃ የፖለቲካ ምህዳሩን በማጥፋቱ እንጂ እነዚህን የፓለቲካ ሃይሎች ሚረዱ ሁሉ፡  ኤርትራን ጨምሮ ስለፈለጉ ሊሆን አይችልም። ጭቆና ባለበት ጭቆናን የሚታገሉ ሃይሎች መኖራቸው ተፈጥሯዊ እውነታ ነው። የነዚህን ሃይሎች ተጽዕኖ ለመቀነስና ጨርሶውኑ ለማጥፋት የደህንነት ፖሊሲ አይነቶች ቢደረደሩ ምንም የሚፈጥረው ፋይዳ የለም። የነዚህ ሃይሎች የህልውና መሰረት ስርዓቱ የፈጠራቸው ዘርፈ ብዙ “የፖለቲካ ችግሮች“ ናቸው። የስርዓቱ ጸረ ህዝብነትና ጸረ ዲሞክራሲያዊነት እስካለ ድረስ በየፊናው የሚደረገው ትግል እያደገና እየሰፋ እንደሚሄድና ህዝቡ ከዚህ አስከፊ ቀንበር ነጻ ለመውጣት ምንም አይነት መስዋዕትነትን ከመክፈል ወደኋላ እንደማይል ጄኔራሉ የሚጠፋቸው አይመስለኝም።
(ይቀጥላል)
ነጻነት ቡልቶን ቀጥሎ ባለው የኢሜልና ፌስቡክ አድራሻ ማግኘት ትችላላችሁ

ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የኢትዮጵያ ምድር ላይ ልዩ ጥቅም አለው! የሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ የሕወሓት ሀገር ከፋፋይ ቀጣይ አጀንዳ አካል ነው source zehabesha

(የጉዳያችን ማስታወሻ)
ጉዳያችን / Gudayacnhn
ሰኔ 21/2009 ዓም (ጁን 28፣2017)
++++++++++++++++++++
ዛሬ ሰኔ 20፣2009 ዓም የሕወሓት ሚኒስትሮች ምክር ቤት የኦሮምያ ክልል በአዲስ አበባ ላይ የሚኖራት ጥቅም በሚል ርዕስ ውሳኔ ማሳለፉ እና የሕወሓት ኢህአዴግ  99% አሸነፍኩ ወዳለበት ምክር ቤት እንደሚመራ ተነግሯል። ጉዳዩ ልዩ መብት የሰጠ የመሰለው ካለ እርሱ ከ26 አመታት በኃላም ገና ፖለቲካ ሀ ሁ እያለ እንደሆነ መረዳት ያለበት ይመስለኛል።
file photo
1/ ልዩ ጥቅም የሁሉም ኢትዮጵያዊ መብት አይደለም እንዴ?
 
ልዩ ጥቅም የሚለው አባባል በእራሱ የመከፋፈል አላማ ያነገበ አባባል ነው።አንድ ሰው ልዩ ጥቅም ለማግኘት ዋናው መሰረት ሊሆን የሚገባው በኢትዮጵያዊነቱ ነው እንጂ የታሪክ የበላይነት ወይንም የዘር መሰረቱ ወይንም የተለየ አነጋገር በመናገሩን መሰረት አድርጎ የሚሰጥ ከሆነ መከፋፈል ነው።ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የኢትዮጵያ ምድር ላይ ልዩ ጥቅም ሊኖረው ይገባል። ልዩ የሚያደርገው ደግሞ ከኢትዮጵያ ምድር በመውጣቱ ነው።ከጃፓን ወይንም ብራዚል የመጣ ሰው የማይኖረው ልዩ ጥቅም ኢትዮጵያዊ ሊኖረው ይገባል።ይህ ማለት ኦሮሞው አዲስ አበባ ላይ በኢትዮጵያዊነቱ ልዩ ጥቅም እንደሚኖረው ሁሉ አዲስ አበቤውም በኦሮምያ ላይ ልዩ ጥቅም አለው።ኦሮሞው በመቀሌ ላይ ልዩ ጥቅም እንደሚኖረው ሁሉ የአክሱሙም ሰው በኦሮምያ ላይ ልዩ ጥቅም አለው።የወለጋው ገበሬ በጎንደር ላይ ልዩ ጥቅም እንዳለው የራስ ዳሽን ገበሬም በነቀምት ላይ ልዩ ጥቅም አለው።ይህ ሁሉ ልዩ ጥቅም የሚመነጨው እንደ ህወሓት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በከፋፋይ አጀንዳ ላይ የተመሰረተ ሳይሆን በኢትዮጵያዊነት ሙሉ መብት ሁሉም የኢትዮጵያ ዜጋ እና መሬት በሁሉም የኢትዮጵያ መሬት ላይ ልዩ ጥቅም አለው።የኦሮምያ ልዩ ጥቅም በአዲስ አበባ የሚለው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ውሳኔ  በእራሱ ከፋፋይ የሆነው  የስርዓቱ አጀንዳ ቀጣይ ምዕራፍ ነው።
2/ የውሃ ፍሳሽ አገልግሎት ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚሰጥ አገልግሎት አይደለም እንዴ?
 “የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ አገልግሎት በአዲስ አበባ ዙርያ ላሉ የኦሮምያ ክልሎች ያካተተ ይሆናል” ይላል ከአዋጁ አካል ውስጥ አንዱ።አሁንም ውሃ የማግኘት ልዩ መብት የሁሉም ኢትዮጵያዊ መብት ነው።ይህ አዋጅ ባይወጣ ኖሮ በኢትዮጵያዊነቱ በአዲስ አበባ ዙርያ ያሉ የኦሮምያ ክልሎች የውኃ አገልግሎት ላያገኙ ነበር? የውኃ ፍሳሽ አገልግሎት ለማግኘት የልዩ ጥቅም አዋጅ ባይወጣ ኖሮ በኢትዮጵያውነታቸው የማግኘት መብት የላቸውም ነበር? ይህ በእራሱ ከፋፋይ አቀራረብ ነው።በአዲስ አበባ ዙርያ ያለ የኦሮሞ ሕዝብ ውሃ ለማግኘት ልዩ አዋጅ መጠበቅ ነው ያለበት ወይንስ በኢትዮጵያዊነቱ የሚያገኘው መብት ነው መሆን ያለበት? ለአዲስ አበባ ውሃ ፍሳሽ አገልግሎት ወጪ የሚሸፈነው  ቀረጥ  ከኦሮምያ የሚመጣ ገንዘብም ጭምር መሆኑን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሊያረሳሳን ነው ? እናስ የአዲስ አበባ ዙርያ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ገና ለገና ከአዲስ አበባ ሕዝብ ጋር አብሮ ይነሳብኛል ልከፋፍለው በሚል እሳቤ ውሃ በልዩ ጥቅም አዋጅ መሰረት ይዘረጋልሃል የሚል አዋጅ ረቂቅ አንድ ሐሙስ የቀረው እና የታመመ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ካልሆነ ማን ያወጣዋል?
3/ የጤና አገልግሎትስ የሁሉም ኢትዮጵያዊ መብት አይደለም እንዴ?
 
በአዋጁ ረቂቅ ላይ “አዲስ አበባ ወይም ፊንፊኔ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ በመሆኗ በከተማዋ የሚሰጠው የጤና አገልግሎት በከተማዋ ዙሪያ ያሉ የክልሉ ተወላጆችን ታሳቢ ያደረገ ይሆናል” ይላል። የጤና አገልግሎት የኢትዮጵያዊነት ልዩ ጥቅም ነው።ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍልል ቢኖር የጤና አገልግሎት የማግኘት መብቱ ነው።በእዚህ ረቂቅ ላይ አዲስ አበባ እና ኦሮምያ የተለያዩ ሀገሮች ይመስል በአዲስ አበባ የሚሰጠው የጤና አገልግሎት በከተማዋ ዙርያ ያሉ የክልሉ ተወላጆች ታሳቢ ያደርጋል ሲል ዛሬ ተነስቶ ልዩ ጥቅም የሰጠ አስመስሎ ሕዝብ የመከፋፈል አላማ ለማሳካት ብቻ የተገለፀ ነው።
4/ የአዲስ አበባ ሕዝብ እና የኦሮምያን ሕዝብ ከህወሓት በበለጠ ይተዋወቃል 
በእዚህ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአዲስ አበባ ስም በፊንፊኔ፣የከተማዋ አንዳንድ ቦታዎች እና አደባባዮች በኦሮምያ ታሪክ ይቀየራሉ የሚል ሃሳብ የያዙ አረፍተ ነገሮች እንዲሁም ኦሮምኛ ከአማርኛ ጋር የስራ መጠቀምያ ይሆናል ይላል።ኦሮምኛ የስራ መጠቀምያ መሆኑ አማርኛ እስካልገባው ድረስ ኦሮምያ የተወለደ ኢትዮጵያዊ በኦሮምኛ አገልግሎት ማግኘቱ ሙሉ መብቱ ነው።ዛሬ ህወሓት እንደ ልዩ ጥቅም አድርጎ ማቅረቡ ነው የማይመቸው። ይህ እንዴት ልዩ ሆኖ ይቀርባል? ኢትዮጵያዊ መብቱ በሚለው ስር የሚገባ ነው።አንድ የጋምቤላ ተወላጅ አዲስ አበባ መጥቶ አማርኛ ካልገባው በጋምቤላ አነጋገር አገልግሎት የማግኘት መብቱ ኢትዮጵያዊነቱ ያጎናፀፈው መብት ነው እንጂ ልዩ መብት ሊባል ያችልም። ሕወሓት ለመከፋፈል ስትፈልግ ልዩ መብት ብላ ትርክት መጀመሯ አስቂኝ ነው። የአዲስ አበባ ስያሜ መቀየር እና የከተማዋን ታሪካዊ ቦታ ከመቀየር አንፃር የተነሳው አገላለጥ በእራሱ የተደናበሩ ሰዎች ያወጡት ረቂቅ አዋጅ ነው። በመጀመርያ ደረጃ በአዲስ አበባ ውስጥ የተሰጡት ስሞችም ሆኑ የአዲስ አበባ የእራሷ ስያሜ እውን ታሪካዊ አመጣጥ የሌለው ባዶ ትርክት ከነበረ የታሪክ ሰዎች ይንገሩን እና እንመን።በሐሰት ታሪክ ግን የትም ሀገር ስም አይቀየርም። ይህንን ልሞክር የሚል ካለ የመስቀል አደባባይ እና የአብዮት አደባባይ ስያሜን ማስታወስ ነው።በሕልም እና በስሜት ሕዝብ ያጋጭልኛል ከሚል እሳቤ ብቻ ሕወሓት ይህንን ማሰቧን እራሱ የኦሮሞ ሕዝብ እና የአዲስ አበባ ነዋሪ ጠንቅቆ ይረዳል።
ባጠቃላይ ልዩ ጥቅም በሚል ቡልኮ የተሸፈነው የህወሓት ሚኒስትሮች ምክር ቤት ረቂቅ አዋጅ አዲስ አበባ እና ኦሮምያን የተለያዩ ሀገር በማስመስል የአዲስ አበባ እና ዙርያዋን ያሉት የኦሮምኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን ግንኙነት ኢትዮጵያዊ የሆነ የጋራ እሴት ሳይሆን የጥቅም ግንኙነት ብቻ ያላቸው  አስመስሎ የማቅረብ ሙከራ ነው።መንግስት የተባለ አካል የመጀመርያ ስራው ዜጎቹን በእኩልነት የማስተዳደር፣ሕግ የማውጣት እና የማስፈፀም አቅሙን የማስመስከር  መሆን ይገባው ነበር።ከእዚህ ውጭ አንዱን አስነስቶ በእዚህ አካባቢ ልዩ ጥቅም አለህ።አንተኛው ግን በምትኖርበት ከተማ ከእርሱ ያነሰ ጥቅም ነው የምታገኘው የሚሉ አባባሎች በእራሳቸው ህዝብን ለመከፋፈል የሚደረጉ አጀንዳዎች የማስቀጠል ሥራ አካል ካልሆኑ ሌላ ሊሆኑ አይችሉም። አዲስ አበባ እና ኦሮምኛ ተናጋሪውን ኢትዮጵያዊ ለመከፋፈል አትሞክሩ።ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የኢትዮጵያ ምድር ላይ ልዩ ጥቅም ሊኖረው ይገባል። ሕዝብ የምታገለውም ሁሉም ኢትዮጵያዊ በኢትዮጵያዊነቱ እኩል ልዩ ጥቅም እንዲኖረው ነው።
ይህንን ፅሁፍ የምደመድመው አንድ የኦሮሞ ማኅበረሰብ አክቲቪስት በተናገረው ንግግር ነው። አባበሉ አሁን ሕወሓት እየዳከረበት ካለው የመከፋፈል ከንቱ ሥራ ፍሬ እንደሌለው በሚገባ ያሳየ ነው። አክትቪስቱ ያለው እንዲህ ነበር
“ሕወሓት የኦሮሞ ማሕበረሰብ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር ያለውን ማኅበራዊ፣ፖለቲካዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ትስስር በመቶዎች በሚቆጠሩ  ዓመታት ውስጥ ያለፈ እና ጠንካራ የደም ትስስር መሆኑን ህወሓት በደንብ ያወቀው አይመስለኝም።እነርሱ ራቅ ካለ አካባቢ ስለመጡ የእዚህ አይነቱ ጠንካራ ግንኙነት ታሪክ በደንብ የገባቸው አልመሰለኝም።የኦሮሞ ሕብረተስብ አሁን ሕወሓት እለያይበታለሁ እያለ የሚያቀርባቸው አጀንዳዎችን የመለያያ አጀንዳዎች እንደማይሆኑ ጥንት በሰራቸው ስርዓቶች ካፈረሳቸው ቆይቷል።ሕወሓት ትልቅ የመረጃ ክፍተት ላይ እንዳለ መረዳት አለብን” ነበር ያለው።