Monday, February 6, 2017

ለፖለቲካዊ ችግሮች ፖለቲካዊ ውይይት!! የጦማሪያንን ሃሳብና አስተያየት ቆንጅት ስጦታው



ከውይይቱ ምን ይጠበቃል?
በሀገሪቱ የተፈጠሩ ተቃውሞና ግጭቶችን ተከትሎ አንጋፋዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከገዥው ፓርቲ ጋር የድርድርና ውይይት መድረክ እንዲዘጋጅላቸው በተደጋጋሚ መወትወታቸው አይዘነጋም፡፡
የመጀመሪያው የድርድርና የውይይት መድረክም ባለፈው ሳምንት በፓርላማ ተካሂዷል። አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውይይቶቹና ድርድሮቹ ለመገናኛ ብዙኃን ፍጆታ የሚውሉና የይስሙላ እንዳይሆኑ
ስጋት ቢኖራቸውም አብዛኞቹ በመድረኩ መዘጋጀት ደስተኞች ናቸው። ውይይቱ በታቀደው መሰረት በተከታታይ የሚቀጥል ከሆነ፣ እያንዳንዱ ፓርቲ የውይይት አጀንዳዎቹን ማቅረብ ይጠበቅበታል፡፡
ለመሆኑ ተቃዋሚዎች ከኢህአዴግ/መንግስት ጋር መወያየት ያለባቸው በምን ጉዳዮች ላይ ነው? ሂደቱስ? ከውይይቱ ምን ይጠበቃል? ከተወያዮቹስ?
“የተቃዋሚዎችን የመደራደር አቅም እጠራጠራለሁ”
አጥናፈ ብርሃኔ (ጦማሪ)
የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋትና ትንሽ መላወሻ ቦታ የሚያመጣ ከሆነ፣ ድርድሩን እንደ መልካም ውጤት አድርጌ ነው የምወስደው፡፡ አሁን የሚደራደሩት ፓርቲዎች ይሄን ለማድረግ ከቻሉ ትልቅ ነገር ነው፡፡
ኢህአዴግስ እውነት የሚያምንበትን ነው እያደረገ ያለው? በሚለው ላይ ጥርጣሬ አለኝ፡፡ ከዚህ ቀደም የተደረጉ ድርድሮች አሉ፡፡ የምርጫ ስነ ምግባርን በተመለከተ ድርድር ተደርጓል፡፡ ግን ምን ውጤት አመጣ? ያ ድርድር ለማን ነው የጠቀመው? ከዚያ ድርድር በኋላ በምርጫ ምን ውጤት መጣ? ይሄ መመርመር አለበት፡፡ ይህ የምርጫ ስነ ምግባር ድርድር ላልተደራደሩ ፓርቲዎች ማነቆ ሆኖ ነበር። ብዙ ተጎድተውበታል። ችግሮችን ሲፈጥርባቸው ነበር፡፡ አሁን ላይም ተቃዋሚዎቹ የመደራደር አቅማቸውን እጠራጠራለሁ፡፡ ከዚያ ውጪ ገዥው ፓርቲ እስካሁን ምንም አይነት መለሳለስ እያሳየ አለመሆኑ ሌላው ተግዳሮት ነው።
የአድርባይነት ስሜት የህዝብን አመኔታ የሸረሸረ በመሆኑ የገዥው ፓርቲ መጠቀሚያ እንዳይሆኑ ነው የምሰጋው፡፡ አቅም ኖሯቸው መደራደር ቢችሉ እንዲደራደሩባቸው ከሚያስፈልጉ ጉዳዮች ዋናው፡- ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ ጉዳይ፣ የፖለቲካ መጫወቻ ሜዳው መጥበብ፣ የፖለቲካ እስረኞች ጉዳይ ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር መረራን ጨምሮ በእስር ላይ የሚገኙ የመድረክ አመራሮች ካሉ፣ እነሱ መፈታት በሚችሉበት ጉዳይ ላይ መደራደር አለባቸው፡፡ በግሌ ውጤት ያመጣል ብዬ ባልጠብቅም ውጤቱን ከሂደቱ መጠበቅ አለብን፡፡
—————————————-
“ሀገር በድርድር ነው የሚገነባው”
አቤል ዋበላ (ጦማሪ)
እንደ ሀገር ባለፉት ሁለት ስርአቶች የተፈፀሙ ስር ነቀል ለውጦች ብዙ ዋጋ አስከፍለውናል፡፡ ስር ነቀል ሲሆን ብዙ ነገር ወደ ኋላ ይመለሳል፡፡ አሁንም ቢሆን ስር ነቀል ለውጥ የሚታለም ከሆነ፣ለህዝቡ የተሻለ ለውጥ ያመጣል ብዬ አላስብም፡፡ ያለውን ስርአት ለማስተካከል ንግግሩ መጀመሩ በራሱ ጥሩ ነው ብዬ ነው የማስበው፡፡
ድርድር ሲባል የሚታወቀው በተመጣጣኝ ኃይሎች መካከል የሚደረግ ነገር ነው፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ እውነታ፣ተቃዋሚው በመንግስት በደረሰበት ተደጋጋሚ ጫና በጣም ተዳክሞ ነው የሚገኘው፡፡ ድርድሩ የምር ችግር ፈቺ እንዲሆን ከተፈለገ፣ በተቃዋሚው ወገን ያለውን የኃይል መሳሳት የሚቀንስ መሆን አለበት፡፡ ተቃዋሚው እንደፈለገ ህዝቡን በዙሪያው እንዲያሰባስብ ክፍት መሆን አለበት፡፡ መሪዎቻቸው የታሰሩባቸው ፓርቲዎች አሉ፡፡ እነዚህ መሪዎቻቸው እንዲለቀቁላቸው ያስፈልጋል፡፡ ይህ ከሆነ ተቃዋሚዎችም በህዝብ ዘንድ ያላቸው አመኔታ ስለሚጨምር ድርድሩ አቅምና ውጤት እንዲሁም ተአማኒነት ይኖረዋል፡፡ ድርድራቸውን በሚዲያዎች አጠቃቀም፣በፍትህና ዲሞክራሲ ጉዳዮች ላይ ቢያደርጉ የበለጠ ውጤት ማምጣት ይቻላል፡፡
ኢህአዴግ ለፖለቲካ ትርፍ ሲል ብዙ ጥፋቶች ሰርቷል፡፡ አሁን ግን ስልጣንን የማዳን ሳይሆን ሀገርን የማዳን ስራ ነው መስራት ያለበት፡፡ ይህ ድርድር የዚህ አይነት ውጤት ይዞ መምጣት አለበት፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም እንደ ፊጋ በሬ ኢህአዴግን ሳያስደነግጡት፣ በአግባቡ በኃላፊነት ስሜት ሊደራደሩ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡ ኢህአዴግም ይሄን እድል ማባከን የለበትም፡፡ ሀገር በድርድር ነው የሚገነባው፡፡
————————————
‹‹ድርድሩ በቅንነትና በቁርጠኝነት መካሄድ አለበት››
በላይ ማናዬ (ጦማሪና ጋዜጠኛ)
ድርድሩ ከልብ የሚካሄድ ከሆነ መልካም ነው። በተለያየ አጋጣሚ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችም ሆኑ ሌሎች በሃገራቸው ጉዳይ ይመለከተናል የሚሉ ሰዎች ሲጠይቁት የነበረው የነበረው ይሄንኑ የድርድና የውይይት መንገድ ነው፡፡ የጋራ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ከልብ መነጋገር፣ መደራደር በየትኛውም ሁኔታ የሚደገፍ ነው፡፡ እኔ በግልም በተደጋጋሚ በፅሁፎቼ ስጠይቅ የነበረው መነጋገር ወሳኝ እንደሆነ ነበር። ይሄ ድርድርና ውይይት ግን ቅንነት በተሞላበት መንገድ፣ በደንብ ችግሮችን እያነሱ በጥንቃቄ መካሄድ አለበት። እንዲሁ ለይስሙላ የአንድ ሰሞን ጫጫታ ብቻ ሆኖ እንዳያልፍ በአንክሮ መከታተል ያስፈልጋል፡፡
በዚህ ድርድር ላይ በተቃዋሚዎች ቢነሳ ብዬ የማስበው፣ በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት ለእስር ተዳርገውብናል ያሏቸው ሰዎች እንዲለቀቁ፣ የፓርቲ አመራሮች፣ ጋዜጠኞች፣ ብሎገሮች ታስረዋል፤ እነዚህ ተፈተው የድርድሩ አካል መሆን አለባቸው። በትክክል የድርድሩ አካል መሆን ያለባቸው የታሠሩ የፖለቲካ አመራሮች አሉ፤ እነሱ እንዲሳተፉ መጠየቅ አለባቸው፡፡ ሌላው ከህገ መንግስቱ ተፃራሪ ናቸው እየተባሉ በህግ ባለሙያዎች አስተያየት ይሰጥባቸው የነበሩ ህጎች ላይ ጠለቅ ያለ ድርድር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዶቹ በህግ ባለሙያዎች ተጠንተው ቢሰረዙ ምኞቴ ነው፡፡ ከኢህአዴግ ጋር በሚደረገው ድርድር ተቃዋሚዎች የህዝቡን ሃሳብና ስሜት በማንፀባረቅ ከልባቸው ሊሰሩ ይገባል ብዬ አምናለሁ፡፡ መንግስት ቁርጠኝነቱን እስከ መጨረሻው የሚቀጥል ከሆነ ጥሩ ነው፡፡ ግን በተደጋጋሚ ካየነው ልምድ ስንነሳ፣ ቁርጠኝነቱ እስከ ምን ድረስ ነው በሚለው ላይ ጥርጣሬ ያድርብኛል። ግን ካለመነጋገር መነጋገሩ የተሻለ በመሆኑ ጠንክሮ መደራደሩ የተቃዋሚዎች ሚና ነው ብዬ አምናለሁ። በሌላ በኩል በድርድሩ የተገለሉ የፖለቲካ ሃይሎች እንዳይኖሩ ቢደረግና ሁሉንም አካታች ቢሆን መልካም ውጤት ያመጣል፡፡
የህዝቡ ድምፅ በሙሉ እንዲሠማ ከተፈለገ፣ አሁን ካሉት ፓርቲዎች በተጨማሪ ሌሎች ያገባናል የሚሉም መካተት አለባቸው፡፡ በዚህ መንገድ የሚካሄድ ከሆነ፣ ድርድሩና ውይይቱ ውጤት ሊያመጣ ይችላል የሚል ተስፋ አለኝ፡፡
——————————
‹‹በድርድሩ ሁሉም እኩል መሆን አለባቸው››
ናትናኤል ፈለቀ (ጦማሪ)
በአንድ አካል መልካም ፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ፣ ሌሎች ደግሞ ተለማማጭ ሆነው የሚካሄድ ድርድር ትክክለኛ ውጤት አያስገኝም። ድርድር ከተባለ ሁሉም በእኩልነት መጥተው፣ ለሁሉም ምቹ የሆነ ውጤት እንዲኖረው ነው የሚፈለገው፡፡ ነገር ግን አንዱ የፈለገውን ማድረግ የሚችል፤ ሌሎቹ ደግሞ አሉ ለመባል ያህል የሚገቡበት ድርድር የአንደኛውን ወገን ብቻ ፍላጎት ይዞ እንደሚጠናቀቅ መተንበይ ቀላል ነው። እኔ ለምሳሌ “ከዚህ ድርድር መልካም ውጤት ትጠብቃለህ ወይ?” ብባል፣እንድጠብቅ የሚያደርገኝ ነገር ስላላየሁ አልጠብቅም፡፡ ከዚህ በፊትም እንዲህ ያለው ነገር በተለያዩ ስሞችና ቅርፆች ተሞክሯል፤ ግን ምንም የተለየ ነገር አላመጣም፡፡ ይሄም ያመጣል ብዬ አልጠብቅም፡፡
በድርድሩ ለምሳሌ “ህገ መንግስቱ ይከበር” የሚባል ከሆነ ምንም አዲስ ነገር የለውም፡፡ ዋናው ተግባር ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ተደራድረው ቢለያዩ፣ አንደኛው ወገን ስልጣን ሁሉ በእጁ ያለ በመሆኑ ስምምነቱን እንደፈለገ ሊጠቀምበት ይችላል፡፡ ግን ድርድሩ የታሠሩ ፖለቲከኞች ይፈቱ፣ ሚዲያው ነፃ ይሁን፣ የፖለቲካ ስልጣን እንጋራ —– ከሆነ ጥሩ ሊሆን ይችላል፡፡ ፓርቲዎቹ የምርጫ ስርአቱ ላይ ብቻ ተደራድረው ሊወጡም ይችላሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ያን ያህል ውጤት የለውም፡፡ በየትኛውም ሥርዓት ውስጥ በሃቀኝነትና በቁርጠኝነት ከተሰራ ለውጥ ይመጣል፡፡ ስለዚህ መንግስት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ሊያደርግባቸው በሚገቡ ጉዳዮች ላይ አጠንክረው ቢደራደሩ ነው መልካም የሚሆነው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በፖለቲካ መሳተፍ አስፈሪ በሆነበት ሰዓት የተፈጠሩ ፓርቲዎች በመሆናቸው፣ይብዛም ይነስም በዚህ ድፍረት ውስጥ ያሉ ፓርቲዎችን ልናበረታታ ይገባል፡፡ ሌላ ወካይ እስከሌለ ድረስ ህዝቡን ወክለው መደራደር ይችላሉ የሚል እምነትም አለኝ፡፡

Sunday, February 5, 2017

9 የየመን ዜጎች ዶናልድ ትረምፕ ባገዱት የጉዞ እገዳ ምክንያት ከአሜሪካ ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደረገ

Yemeni
አባይ ሚዲያ ዜና
ናትናኤል ኃይለማርያም
ዘጠኝ የመናዉያን ፕሬዚደንት ዶናልድ ትረምፕ ባወጡት የጉዞ እገዳ ምክንያት ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ማድረጋቸዉን እና ጎረቤት አገር ወደ ሆነችዉ ጅቡቲ እንዲላኩ መደረጉን አንድ የወያኔ ባለስልጣን አስታወቀ።
የመን አሜሪካ ለደህንነቴ ስጋት ናቸዉ ብላ ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ እገዳ ከተጣለችባቸዉ ሰባት አገራት ዉስጥ አንዷ በመሆኗ እነዚሁ ተጓጓዦች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ የተደረገዉ ኢትዮጵያ ለጅቡቲ ቅርብ በመሆኗ እና ጅቡቲ በቀይ ባሕር ለምትዋሰነዉ የመን በ20 ማይልስ ወይም በ30 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ አገር ስለሆነች ነዉ በማለት የወያኔዉ አፈቀላጤ ተናግረዋል።
ወደ አዲስ አበባ የተላኩበት ዋናዉ ምክንያት ተብሎ በወያኔዉ አፈቀላጤዉ ነገሬ ሌንጮ የተገለጸዉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዋሽንግቶን ወደ አዲስ አበባ በረራ ስላለዉ ነዉ በማለት ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮችን ሳያነሱ በደፈናዉ መግለጻቸዉ ታዉቋል።
የአሜሪካን ደህንነት ለመጠበቅ በሚል የሰባት አገሮችን የጉዞ እገዳ ያደረጉት ዶናልድ ትረምፕ ምን አልባትም ይኽ ዉሳኔያቸዉ ከፍተኛ የሆነ ሕዝባዊ ተቃዉሞ ሊጋብዝ እንደሚችል እና በአሜሪካ ባሉ በተለያዩ የፌደራሉ ከፍተኛዉ ፍርድ ቤት የአሜሪካንን ሕገ መንግስት የሚጻረር ነዉ ሲሉም ይደመጣሉ።

በቤንሻንጉል የወርቅ ማእድን ማውጫን ለመቆጣጠር በተደረገ ጦርነት 4 የወያኔ ወታደሮች ተገደሉ። ብዛት ያላቸው ቆስለዋል

አባይ ሚዲያ ዜና በዘርይሁን ሹመቴ
በቤኒሻንጉል ጉምዝ የህውሃት ወያኔ ወታደሮች በክልሉ ሸምቀው ከሚታገሉ የነጻነት አርበኞች ጥቃት እንደደረሰባቸው ተሰምቷል።
ይህ ከፍተኛ የወርቅ ክምችት ያለበት ክልል የመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሃብትነት መሆን ቀርቶ በአገዛዙ እና ስርአቱን በመደገፍ በሚታወቁት በሼክ አላሙዲን ስር የሚገኝ ነው።
እንደ ምንጮች ገለጻ መሰረት በሸረቆሌ የሚገኘውን የወርቅ ማእድን በሚብቁ የወያኔ ወታደሮች ላይ በተከፈተ ጥቃት የአገዛዙ ወታደሮች ለጉዳትና ለሞት ተዳርገዋል።
በዚህ የነጻነት ታጋዮች በተከፈተ ጥቃት አራት (4) የህውሃት ወታደሮች መገደላቸውና ቁጥራቸው በዛ ያሉ ደግሞ ለከፍተኛ የአካል ጉዳት እንደተዳረጉ ሪፓርቶች ይገልጻሉ።
እጅግ ከፍተኛ የወርቅ ክምችት ከዚሁ ክልል የሚወጣ ቢሆንም የአካባቢው ተወላጆችና ነዋሪዎች ከጥቅሙ የመጋራት እድል በአገዛዙ ተነፍገዋል።
በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የነጻነት ሃይሎች ይህንን የወርቅ ማእድን ማውጫ አገዛዙ ካሰማራቸው ወታደሮች ለመንጠቅ ደረጉት ውጊያ ሃለፎም እና ወራዊ አብርሃም የሚባሉ የትግራይ ተወላጆች ወታደሮች መገደላቸው ተረጋግጧል።
እንደዚህ ያለው እምቅ የኢትዮጵያ ሃብት በአገዛዙ ባለስልጣናት ብቻ ኢፍትሃዊ በሆነ መልኩ ጥቅም መዋሉ በክልሉ ለሚፈጠረው ተደጋጋሚ የትጥቅ ትግል ዋንኛ ምክንያት ሆኗል።

Friday, February 3, 2017

(ሳተናው) መኢአድ፣ ሰማያዊን ጨመሮ አምስት ድርጅቶች ለድርድሩ በጋራ እየሰሩ ነው



ገዢው ፓርቲ ሕወሃት/ኢሕአዴግ ከተቃዋሚዎች ጋር ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እንወያይ በሚል ያቀረበውን ጥሪ ተከትሎ በአገር ዉስጥ የሚገኙት የተቃዋሚ ፓርቲዎች (ሰማያዊ፣ መድረክ፣ መኢአድ፣ ኢዴፓ፣ ኦራፓ …) ለዉይይት ዝግጁነታቸውን ገልጸው ከሁለት ሳምንታት በፊት ለአንድ ቀን መነጋገራቸው ይታወቃል። በወቅቱ ተቃዋሚዎቹ በዚህ ዉይይትና ድርድር ኢሕአዴግ ስብሰባውን መምራት የለበትም፣ ሌላ ሶስተኛ አካል መኖር አለበት የሚል አቋም በመያዛቸውና ገዢው ፓርቲም ያንን በመቀሉ ፣ ሶስተኛ አካል ማን ይሁን በሚለው ላይ ሁሉም  ሐሳቦች ይዘው ከመጡ በኋላ በሌላ ጊዜ ዉይይት እንዲቀጥል ተወስኖ ነበር።
በዚህ መሰረት ቃዋሚ ፓርቲዎች ድርድር የሚካሄድበትን ስነ-ስርዓት አስመልክቶ አማራጭ ሃሳባቸውን በጋራ ተመካክረው በአንድ ደብዳቤ አስገብተዋል ። 7 ገፅ ያለው ደብዳቤ የእጩ አደራዳሪዎች ስም ጥቆማና የአደራዳሪዎችን ሚና ፣ የእጩ ተዛቢዎችን ጥቆማና የታዛቢን ሚና ፣ የስብሰባ ስነ-ስርዓትንና የዲሲፕሊን እርምጃ አወሳሰድ ፣ ከሚዲየ የሚኖርን ግንኙነትና ውጤት እንዴት ለህዝቡ ይገለፅና ልዩ ልዩ ጉዳዮች የሚልን ያካተተ ነው ።
በጋራ ደብዳቤ የጻፉትም በጋራ ተሰባብሰው የመከሩት ድርጅቶች አምስት ሲሆኑ፣ ስድስት አገር አቀፍና በኢትዮጵያ አንድነት የሚያምኑ ፣ ተመሳሳይ ፕሮግራሞች ያሏቸው ድርጅቶች ናቸው። እነርሱም የሰማያዊ ፓርቲ፣ መኢአድ፣ ኢዴፓ፣ ኢራፓ(የኢትዮዮጵያ ራእይ ፓርቲ)፣ መኢዴፓ(መላው ኢትዮጵያ ዴሞክራቲክ ፓርቲ) እና ኢብአፓ(የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት ፓርቲ) ናቸው።

አርበኛ አብሲቴ – ኄኖክ የሺጥ



አርበኛ አብሲቴ – ኄኖክ የሺጥላ
ሃሳብን መሞገት ሲዳግት ፥ ቀዳዳ ፈልጎ ትንኮሳ አንዳች ለውጥ አያመጣም ። ለምሳሌ ብርሃኑ ነጋ አብሲት እንደሚጥል ተናግሯል ። አብሲት መጣሉ ወንጀል አይደለም ። ከይህ በፊት እንዳልኩት ለጦሩ ሚንስ ቤት ሁነኛ ሰው ሆኖ ሊሰራ ይችላል። አብሲት በመጣሉ አርበኛ አብሲቴ አላልኩትም ! ቢሳካለትም ባይሳካለትም ያው አርበኛ ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ነው የሚባለው። እኔ የተቃወምኩት ስለ አብሲት ያወራበት ሰዓት ጎንደር ውስጥ ሰዉ ትንቅንቅ ላይ በነበረበት ወቅት ነው ! ጎጃም ውስጥ አማሮች ወገኖቻችን ከወያኔ ጋር እየተፋለሙ ባሉበት ወቅት ነው ነው ! ይህንን በመቃወሜ ሙቅ ስለማሞቅ ተከታዮቻቸውን ፥ አልፎ ተርፎ እዚህ ካልፎርኒያ በኪኒን የሚኖሩ በሽተኞችን ሳይቀር እየደጎሙ ፥ ከኔ አልፎ ልጆቼን እና ባለቤትን ፀያፍ በሆነ ቃል ያሰድባሉ። እነሱ ከደሙ ንፁ ለመምሰል ይሞክራሉ ! ዋናው ነገር ግንቦት ሰባቶች እንዴት እንደሚሰሩ አውቃለሁ።
ለምሳሌ እዚህ ሳን ሆዜ የሚኖር አንድ ሃብታሙ የሚባል የኢሃፓ አባል በፅሁፍ ስለተቃወማቸው ብቻ ፥ ይህንን ሰው ከስራው ለማባረር መስራቤቱ ድረስ ደውለው አመልክተዋል ። ይህ ሰው ልጆች አሉት ፥ የዚህ ሰው ከስራ መባረር ልጆቹን ጎዳና ላይ እንዲጥል ያደርገዋል ። በወቅቱ ህንን ለማድረግ ሲያስቡ « እናንተ አብዳችኋል እንዴ ? » ብዬ ተቃውሜያቸው ነበር ። ሃሳቡን ስለገለጠ ከስራ ይባረር ማለት ከወያኔነት በምን ይለያል ? እነዚሁ ሰዎች ቤ/ክ በራፍ ላይ አስተናጋጅ ሆነው ፥ ገቢ ወጪውን ሰላምታ ሲሰጡ ይውላሉ ! አውሬዎች ስለሆነ አምላክ እንኳ የላቸውም !
በመጨረሻ
እኔ መሪ ነኝ አላልኩም ! ስለዚህ መሪ ነኝ ብሎ ስለ ሃብሲት መጣል የሚያወራውን እተቸዋለሁ! እቃወመዋለሁ ! ምክንያቴ ደሞ አላማውን የሳተ ስለመሰለኝ ! ያም ቢሆን አሁንም አርበኛ እብሲቴ ለማለት ግን አልደፍርም ! ነውር ስለሆነ !
እንዲያ ብናየው ጥሩ ነው !
ኄኖክ የሺጥላ

Wednesday, February 1, 2017

ጭንቅ ውስጥ የገባው ወያኔ ለአዲስ ሰራዊት ምልመላ እየለመነ ነው

ሙሉነህ ዮሃንስ
ሳይጀመር እየተጨናገፈበት ያለው የአዲስ ሰራዊት ምልመላ ሁለት አብይ ጉዳይ ገሃድ አውጥቷል። አንደኛ ወያኔ አሁን ባለው ሰራዊት መተማመን አልቻለም። በብዙ ግንባር እንደታየው የውጊያ ሞራሉ የወደቀው ሰራዊት የወያኔን የማይቀር መንኮታኮት ያሳያል። ሁለተኛ ለመጨረሻው ሰአት የቆጠበውን የትግራይ ተወላጅ ሰራዊት ቆጥቦ በየቦታው የተወላጆች የእርስ በርስ እልቂት እንዲቀጥል ይፈልጋል። ይህን ተንኮሉን የተረዳው ወጣት የወያኔን ቅጥር ልመና ሳይጀመር እያከሸፈው ነው።
የኢትዮጵያ ወጣት በብዙ መረጃ እንደምንገነዘበው በየቦታው የተነሱትን ህዝባዊ ትግል ለመቀላቀል ቁርጠኛ ሆኖ መሳሪያ ለመታጠቅ እየተመመ ነው። በተቃራኒው ደግሞ ለንፅፅር እንዲሆናቹህ የተያያዙትን የወያኔ የልመና የወታደር ቅጥር ማስታወቂያወች እዩ።







የአማራ ህዝባዊ ተቃውሞን (#AmharaProtests) ተከትሎ የተቃውሞ ድምጽ በሚያሰሙ ዜጎች ላይ እስርና ወከባው ቀጥሏል







በተቃውሞ ሰልፎች የተሳተፉ ወጣቶችን በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች በገፍ ማሰሩ ተቃውሞዎች በበረቱባቸው ከተሞች ከፍተኛ ነው ፡፡ ለምሳሌ በጎንደር ከተማ በሚገኙ 1ኛ፣ 2ኛ፣ 3ኛ፣ 4ኛ፣ 5ኛ እና 6ኛ ፖሊስ ጣቢያዎች በጠባብ ክፍሎች ውስጥ በአንድ ጣቢያ በአማካይ እስከ 140 ሰዎች እንደሚታሰሩ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ጎንደር ከተማ ውስጥ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ለሁለት ሳምንታት ታስሮ የነበረ ወጣት ደረጀ ጌቱ (ስሙ የተቀየረ) እንደሚናገረው በጣቢያው ውስጥ አብረውት ታስረው የነበሩት አብዛኞቹ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ መሳተፋችሁ በፎቶ ተረጋግጧል በሚል ለእስር ተዳርገው የነበሩ ናቸው፡፡
በተመሳሳይ በባህር ዳር ከተማ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች እንዲሁ በከተማዋ ተደርጎ በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት በተሳተፉ ወጣቶች በገፍ እየታሰሩ ነው፡፡ እነዚህ ወጣቶች አንዳንዶቹ በአጭር ጊዜ ሲታሰሩ እና ሲፈቱ ሌሎች ደግሞ በተደጋጋሚ መታርና መፈተታ እንደሚገጥማቸው ማየት ተችሏል፡፡
በእነዚህ ፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩትን ማን እንደታሰረና፣ የት እንደታሰረ ቤተሰብና ዘመድ የማወቅ እድል ቢኖረውም ሌሎች የት እንደታሰሩ ሳይታወቅ ለቀናት፣ ለሳምንታትና ለወራትም የሚከርሙ መኖራቸውም ታውቋል፡፡ እነዚህ የእስር ስፍራዎች በይፋ የማይታወቁና በተቃውሞ እንቅስቃሴው እጃቸው በሰፊው አለበት በሚል መንግስት የጠረጠራቸውን “የሚመረምርባቸው” ናቸው፡፡
ከእነዚህ ድብቅ የእስር ቦታዎች መካከል ለምሳሌ ባህር ዳር አባይ ማዶ ከብአዴን ጽ/ቤት ጀርባ የሚገኝ ቀድሞ የመሳሪያ መጋዘን የነበረ ስፍራ ይገኝበታል፡፡ በዚህ ቦታ የሚታጎሩ ወጣቶችን ቤተሰቦቻቸው ለመጠየቅም ሆነ በዚያ ስፍራ ስለመኖር አለመኖራቸው ለማወቅ እንደማይችሉ ታስረው የተፈቱና፣ ታስረው እንደነበርም እንዳይናገሩ ማስፈራሪያ ደርሷቸው የወጡ ይመሰክራሉ፡፡ አበበ አስረስ (ስሙ የተቀየረ) በዚህ ድብቅ የእስር ቦታ ለ17 ቀናት ሲሰቃይ ቆይቶ መለቀቁን ይናገራል፡፡
‹‹ቦታው የሆነ መጋዘን ነገር ነው፤ ሰፊ አዳራሽ ነው፡፡ በዚህ አዳራሽ ውስጥ በጣም ብዙ ሰዎች አብረውኝ ታስረው ነበር፡፡ የእስራችን ምክንያት ብለው የነገሩን ባህር ዳር ነሐሴ 01/2008 ዓ.ም በነበረው ሰላማዊ ሰልፍ ወቅት ሰልፉን አደራጅታችኋል የሚል ነው፡፡ በእስራችን ጊዜ ቤተሰቦቻችን አንድም ቀን አላገኙንም፡፡ በኋላ ብዙዎችን ወደ ብርሸለቆ ሲወስዷቸው እኔን ድጋሜ ሰልፍ ላይ ካገኘንህ እንገድልሃለን ብለው ዝተውብኝ የሆነ ወረቀት ላይ አስፈርመው ለቀውኛል፡፡ ማታ ላይ ነው በመኪና ከሌሎች ሦስት ልጆች ጋር ጥለውኝ የሄዱት›› ሲል ያስታውሳል አበበ፡፡
አበበ አስረስ ከድብቅ እስር ቤቱ መፈታቱን ተከትሎ ዘመድ ለመጠየቅ በሚል ከአካባቢው ዞር ለማለት አስቦ የቤተሰቦቹን ምክር ተቀብሎ ወደ አዲስ አበባ ዘመድ ጋር ሳምንታትን አሳልፏል፡፡ ‹‹በጣም ከባድ ጊዜ ነበር እስር ላይ ሆኜ ያሳለፍኩት›› የሚለው አበበ፣ ከሳምንታት የአዲስ አበባ ቆይታ በኋላ የገና በዓልን ከቤተሰቦቹ ጋር ለማሳለፍ ወደ ባህር ዳር በተመለሰበት ወቅት፣ ‹‹የት ጠፍተህ ከርመህ እንደመጣህ እናውቃለን!›› በሚል በድጋሜ ለእስር እንደተዳረገ ታውቋል፡፡
በድብቅ እስር ቤቶችም ሆነ በፖሊስ ጣቢያዎች የሚታሰሩ ሰዎች የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጸም ለማረጋገጥ የተቻለ ሲሆን፣ በተለይ ድብደባ በብዙዎቹ ላይ በምርመራ ወቅት የሚፈጸም የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው፡፡ በባህር ዳር ከተማ 9ኛ ፖሊስ ጣቢያ የሚታሰሩ የፖለቲካ እስረኞች በምርመራ ወቅት ጥፍርን እስከመንቀል የሚደርስ ኢ-ሰብዓዊ የሆነ ድርጊት ይፈጸምባቸዋል፡፡
ብዙዎች በፖሊስ ጣቢያ ለሳምንታት እንዲቆዩ ከተደረገ በኋላ ወደ ብርሸለቆ የወታደራዊ ማሰልጠኛ ተቋም ለ‹ተሃድሶ ስልጠኛ› ተግዘዋል፡፡ በማሰልጠኛ ተቋሙ በሚኖራቸው ቆይታም ቢሆን ተመሳሳይ፣ አንዳንዴም የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል፡፡ (በተሃድሶ ማሰልጠኛ ስፍራዎች ስለሚፈጸም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ፕሮጀክት በቅርቡ ለማሳያነት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት መመልከት ይቻላል፡፡)
በአማራ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት በዋናነት ቀድሞውንም በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ በሚታገሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ ያነጣጠረ የእስር እርምጃ ሲወስድ ታይቷል፡፡ በተለይ በክልሉ በስፋት በሚንቀሳቀሱት የሰማያዊና መላው ኢትዮጵያ አንድነት ( መኢአድ) ፓርቲዎች አባላት ለእስር ተዳርገዋል፡፡ ብዙዎች በየአካባቢው በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች ታስረው ሲገኙ፣ አንዳንዶች ደግሞ ወደፌደራል ወንጀል ምርመራ ማዕከላል (ማዕከላዊ) ተላልፈው ጥቂቶች የሽብር ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡
ፕሮጄክታችን ባደረገው ተጨማሪ ማጣራት ከብዙዎቹ መካከል የሚከተሉትን የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አክቲቪስቶች መታሰራቸው የሁኔታውን አሳሳቢነት ያሳያል በማለት አቅርበነዋል፡፡
*ከአማራ ህዝባዊ የተቃውሞ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ ለእስር ተዳርገው የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው:-
1. ንግስት ይርጋ…………… የመብት ተሟጋች፣ አድራሻ ጎንደር…. ቃሊቲ እስር ቤት ታስራ ትገኛለች
2. አለምነው ዋሴ……………የመኢአድ አባል……….አድራሻ ጎንደር….. ቂሊንጦ በእስር ላይ ያለ
3. ቴዎድሮስ ተላይ……….አድራሻ ጎንደር……………………………………. ›› ››
4. አወቀ አባተ……………….የመኢአድ አባል……………………………… ›› ››
5. በላይነህ አለምነህ……………የሰማያዊ ፓርቲ አባል፣ አድራሻ ባህር ዳር……. ›› ››
6. ያሬድ ግርማ…………………. የመኢአድ አባል…………………………………>>
7. አታላይ ዛፌ
*ክስ ሳይመሰረትባቸው በእስር ላይ የሚገኙ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት
7. ማሩ ዳኛው
8. ቢሆን
9. መልካሙ ታደለ
10. ሲሳይ ታፈረ
11. ወርቁ ጥላሁን
12. ድንቁ
13. ስማቸው ማዘንጊያ
14. እያዩ መጣ
15. ድርሳን ብርሃኔ
16. አንዳርጌ አባይ
17. ዮናስ ሰለሞን
18. መሃመድ ኑርየ
19. መምህር መሃመድ አሊ
20. መንግስቴ ብርሃኔ
21. ጌታነህ ደምሴ
22. ታደለ እንዳልፈራ
23. መምህር ለወየሁ ጌቱ
24. እሸቴ ደረሰ
25. ጌጤ ላሽተው
26. ሰይዒድ እንድሪስ
27. አህመድ በዛብህ
28. ጀማል ኡመር
29. አብደላ መሃመድ
30. አዲሱ ጌታነህ
31. ዘሪሁን እሸቱ
32. ጀማል ይመር
33. አበበ ጥላሁን
34. ተሻገር ወልደሚካኤል
35. እያሱ ሁሴን
36. በላቸው አወቀ
37. ዘውዱ ነጋ
38. ወልደመስቀል ማማየ
*የህዝቡን የመብት ጥያቄ (ህዝባዊ ተቃውሞ) ደግፋችኋል በሚል ከታሰሩት መካከል፡-
39. ገድፍ ጌታነህ……ሰሜን ጎንደር በለሳ ወረዳ
40. ሊቀሊቃውንት እዝራ (ቤተ-ክርስቲያንን ሽፋን አድርገው የህዝቡን ተቃውሞ ይደግፋሉ በሚል የታሰሩ)
41. ቀለመወርቅ ዓለሙ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የጎንደር ሀገረ ስብከት ጳጳስ ኃላፊ)
42. ሂሪያኮስ አበበ…..ጎንደር ከተማ
43. ዶ/ር ጋሹ ክንዱ
(ዶ/ር ጋሹ ክንዱ የቡሬ ዳሞት ሆስፒታል ሜዲካል ዳሬክተር ናቸው፡፡ ታህሳስ 27/2009 ዓ.ም ለገና በዓል ወደ ቤተሰቦቻቸው ባመሩበት ጊዜ ባህር ዳር ከተማ ለእስር ተዳርገው ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ እንዲዛወሩ ተደርገው በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡) የፕሮጀክታችንን የአማራ ህዝብ ተቃውሞ እና የመብት ጥሰት ሪፓርት ለማግኘት ይህንን ሊንክ ይጫኑ፡፡
(በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ፕሮጀክት (ኢሰመፕ) የተዘጋጀ)